አዲስ ሪፖርተር – በመሬት መደርመስ አደጋ የተፈናቀሉ ዜጎች ሲደረግላቸው የነበረው ድጋፍ በመቋረጡ፣ ተጠልለው ባሉበት በምግብ፣ በመጠጥና መጠለያ ችግር ላይ መሆናቸው ተመለከተ።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በአሪ ዞን ደቡብ አሪ ወረዳ ኮመር ቀበሌ ሐምሌ 13 ቀን 2017 ዓ.ም በደረሰው የመሬት መደርመስ አደጋ 5 የአንድ ቤተሰብ አባላት ሕይወታቸውን ሲያጡ ከአንድ ሺሕ አራት መቶ በላይ ነዋሪዎች ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ይታወሳል።
የወረዳ ዋና አስተዳደሪ አቶ ግዛው ኃይሉ ለአዲስ ሪፖርተር እንደገለፁት፣ተፈናቃዮች በኃይማኖት ተቋማት ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ መሆናቸውንና ፤ከአደጋው ማግስት በተለያዩ አካላት የተወሰኑ ድጋፍ ከተደረገላቸው በኋላ አሁን ላይ የትኛውም አካል ድጋፍ ማድረግ ማቆሙን ነግረውናል።
በአደጋው ከቤት ንብረታቸው ከተፈናቀሉት ውስጥ ለወሊድ የተቃረቡ ፤ ነፍስ ጥሩ እናቶች ፣ ወላጆች ፣ ልጆች መኖራቸውን ያክላሉ።

ለተፈናቃይ ዜጎች የሚሆን በቂ የእህል፤መጠጥ ፣መጠለያ ፤አልባሳት ፣የሕክምና መሰሪያዎች ፣መድኃኒቶች የአቅርቦት እጥረት ማጋጠሙን ገልፀዋል። የክልሉ እና የዞኑ መንግሥት በቂ የማይባል ድጋፍ እንዳደረጉ ጠቁመው ፤ፌድራል መንግሥት እስካሁን ምንም አይነት ድጋፍ አለማድረጉን ነግረውናል።በመጠባበቂያነት በመጋዘኖች ውስጥ የነበሩ እህል ነክ እና የሕክምና መገልገያ መሳሪያዎች እያለቁ እንደሚገኙ አብራርተዋል።
በተጠቀሱ ምክንያቶች ዜጎች ለከፋ ችግር እንደተጋለጡ ይናገራሉ።አስተዳዳሪው በተጨማሪም ፤የፌድራል ፣የክልል ፣የዞን መንግሥታት እንዲሁም ሌሎች ተራድኦ ድርጅቶች ፣ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች ለተፈናቃዮች የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።






