“ለሕዝባችን ያመጣነው ለውጥ ባለመኖሩ ወደ ዘላቂ የሰላም ስምምነት መጥተናል” ሲል ያስታወቀው የአማራ ሕዝባዊ ፋኖ ድርጅት፣ ከዚህ በሁዋላ በስሙ የሚደረግ የትጥቅ ትግል እንደሌለ አስታወቀ። ገበሬው ወደ እርሻው፣ ተማሪዎች ወደ ትምህርታቸው እንዲመለሱ እንደሚሰራም አመልክቷል።
የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋህድ) የፖለቲካ ዘርፍ ምክትል ኀላፊ እና የወሎ ቤተ አማራ ጠቅላይ ዕዝ የፖለቲካ ዘርፍ ኀላፊ እያሱ አበራ ድርጅቱ የክልሉን ሕዝብ ጥያቄ ለማስመለስ ወደ ትግል ቢገባም የፈየደው ስራ እንደሌለ አመልክቷል “ለሕዝባችን ያመጣነው ለውጥ ባለመኖሩ የሰላም አማራጭን ተጠቅመን ወደ ዘላቂ የሰላም ስምምነት መጥተናል” በማለት ተናግሯል። ካፒቴን ሰጤ ቀደም ሲል “ውሻዬን ሸጬ ቀበሮ ገዛሁ” በማለት የትግሉን አጠቃላይ ግምገማ ማቅረቡና ድርጅቱ በባንዳነት ኢትዮጵያን ሊያፈርሱ ከሚነቀሳቀሱ ግታሪካዊ ጠላቶቿ ጋር መግጠሙን መናገሩ አይዘነጋም።
“ትግሉ በተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ፀረ ሰላም ኃይሎች ጣልቃገብነት አደረጃጀቱ መከፋፈሉን በመጥቀስም ክልሉን እና ሕዝቡን የረጅም ጊዜ የጦርነት ሜዳ አድርገው ለመጠቀም እየሠሩ ነው” ነው ያለው አፋህድ የፖለቲካ ዘርፍ ምክትል ሰብሳቢ፣ ቀደም ሲል አማራ ክልልን የጦርነት አውድማ በማድረግ አገር ለሚበትኑ የሚታወቁ የኢትዮጵያ ጠላቶች ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡ መኖራቸውን የውስጥ መረጃ እያጣቀሱ ሲያቀርቡ የነበሩትን ክፍሎች ግምገማ ሃቀኛነት አመልክተዋል።

የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋህድ) የጎጃም ጠቅላይ ግዛት ዕዝ የፋይናንስ ኀላፊ ከፋለ ዓለሙ ክልሉን ለሁለንተናዊ ቀውስ እየዳረገው የሚገኘውን ጦርነት ለማስቆም ብቸኛው መፍትሔ የሰላም አማራጭ በመኾኑ ችግሮችን በውይይት ወደመፋታት አማራጭ መጥተናል ብለዋል።
ድርጅቱ ከክልሉ መንግሥት ጋር ያደረገው ዘላቂ የሰላም ስምምነት ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ፤ ገበሬዎች ወደ እርሻቸው ፊታቸውን እንዲያዞሩ የሚያስችል እና ለሕዝቡ የሰላም እፎይታን የሚሰጥ መኾኑን ተናግረዋል።
የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋህድ) የጽሕፈት ቤት ምክትል ኀላፊ እና የወሎ ቤተ አማራ ጠቅላይ ግዛት ዕዝ የሕዝብ አሥተዳደር እና ማኅበራዊ ጉዳይ ዘርፍ ኀላፊ ግርማ እጅጋየሁ ሰላምን እናመጣለታለን ብለን ወደ ትግል ለገባንለት ሕዝብ የሰላም እጦት ምንጭ በመኾን ከጉዳት ውጭ ያተረፍንለት ነገር ባለመኖሩ የሰላም አማራጩን ተቀብለን እንደ ድርጅት ወደ ድርድር መጥተናል ነው ያሉት። ከሰላም አማራጭ ውጭ የሚደረግ የትኛውም የትጥቅ ትግል ድርጅቱን የማይወክል መኾኑንም ገልጸዋል።
የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋህድ) ሀገር አፍራሽ ከኾኑ እና ለግል ጥቅማቸው ከሚንቀሳቀሱ አካላት ጋር ድርጅቱ ምንም ዓይነት ኅብረት የሌለው መኾኑን በመግለጽም ከውጭ ኃይሎች ተልዕኮ ተቀብለው የውክልና ጦርነት የሚያደርጉ አካላት ወደ ሰላም አማራጭ እንዲመጡም ጥሪ አቅርበዋል።
ፌስቡክ፡ https://web.facebook.com/addisreporternews/
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter11
X፡ https://x.com/addisreporter
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393






