የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ የዋጋ ግሽበት ጫናው በመቀጠሉ የጠበቀ የገንዘብ ፖሊሲውን ጸንቶ እንዲቀጥል መወሰኑን አስታወቀ። ከዚህ ውሳኔ የደረሰበትን ምክንያት ዘርዝሮ እፖሊሲስውን ለማላላት ምቹ ሁኔታ አለመኖሩንም አመልክቷል።
ኮሚቴው ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም. ባወጣውና ለሚዲያዎች ባሰራጨው መግለጫ እንዳለው፣ የዋጋ ግሽበትን ፣ የፋይናንስ ሁኔታዎችን፣ እንዲሁም የአገር ውስጥና የዓለም አቀፍ ኢኮኖሚያዊ ለውጦችን ከገመገመ በኋላ የዋጋ ንረት እና የኢኮኖሚ አለመረጋጋት በፈጠሩት ጫና ምክንያት የጠበቀ የገንዘብ ፖሊሲ አቋሙን ለማስቀጠል ወስኗል።
የውይይቱ ዋና ትኩረት የነበረው የዋጋ ግሽበት ሲሆን፤ ይህም በተለይ በምግብና በመሠረታዊ ሸቀጦች ዋጋ መጨመር ምክንያት በቤተሰቦች ላይ በቀጥታ ተፅኖ የሚያሳድር ፈተና ሆኖ ቀጥሏል። ኮሚቴው የዋጋ ግሽበቱ ቀደም ሲል ከነበረበት ከፍተኛ ደረጃ የመቀነስ ምልክቶች እያሳየ ቢሆንመ የዋጋ ጫናው አሁንም በከፍተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ደምድሟል። የምግብ ዋጋ ግሽበት ዋነኛውን ድርሻ የያዘ ሲሆን ይህም ከውጭ በሚገቡ ምርቶች ዋጋ እና በውጭ ምንዛሬ ተመን ጫናዎች ተባብሶ በመቀጠሉ በዘህ ወቅት ፖሊሲውን ለማላላት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ አለመኖሩን ገልጿል።
ይህንን ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴው የዋጋ መረጋጋትን ለማረጋገጥ ያለውን ቁርጠኝነት በማጠናከር የባንኩን የማዕከላዊ ወለድ ተመን (National Bank Rate) በ15 በመቶ እንዲቆይ ወስኗል። ይህ ውሳኔ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ቀስ በቀስ በማገገም ላይ ቢሆንም ባንኩ ጥንቃቄ የተሞላበት አካሄድን ለመከተል ያለውን ፍላጎት ያሳያል። በተጨማሪም ኮሚቴው የአጭር ጊዜ ወለድ ተመኖችን ለመምራት እና የገንዘብ ፖሊሲ ውሳኔዎች ወደ ሰፊው ኢኮኖሚ የሚደርሱበትን መንገድ ለማሻሻል የተነደፈውን “የወለድ ተመን ኮሪደር” (Interest Rate Corridor) ማዕቀፍ ጥቅም ላይ እንደሚውል በድጋሚ አረጋግጧል።
ለባንክ ዘርፉ የተላለፈው መልእክት የዲሲፕሊን አስፈላጊነት ላይ ያተኮረ ሲሆን፤ ኮሚቴው ባንኮች ማስቀመጥ ያለባቸው የጥሬ ገንዘብ ክምችት መጠን (Required Reserve Ratio) በ10 በመቶ እንዲቀጥል ወስኗል። ማዕከላዊ ባንኩ በገበያ ውስጥ ያለውን ትርፍ የገንዘብ መጠን (Excess Liquidity) የመምጠጥ ስራውን አጠናክሮ ይቀጥላል። ምንም እንኳን እነዚህ እርምጃዎች ቴክኒካዊ ቢመስሉም ባንኮች ሊያበድሩ በሚችሉት የገንዘብ መጠን እና በብድር ወለድ ዋጋ ላይ በቀጥታ ተጽዕኖ ይኖራቸዋል፤ ይህም ብድር ለሚፈልጉ የንግድ ተቋማት እና ዋና ዋና ግዢዎችን ለሚያቅዱ ቤተሰቦች የራሱ አንድምታ ይኖረዋል።
የውጭ ተጽዕኖዎችም በኮሚቴው ግምገማ ውስጥ በጉልህ ተነስተዋል። የኢትዮጵያ የክፍያ ሚዛን (Balance of Payments) ከከፍተኛ የገቢ ምርቶች ፍላጎት እና ከዕዳ ክፍያ ግዴታዎች የተነሳ አሁንም በጫና ውስጥ ይገኛል። ምንም እንኳን የወጪ ንግድ ገቢ መሻሻል ቢያሳይም የውጭ ተጋላጭነትን ሙሉ በሙሉ ለመቀነስ ገና በቂ አለመሆኑን ኮሚቴው አመልክቷል። በጂኦፖለቲካዊ ውጥረቶች ቀጣይነት ባለው የዋጋ ግሽበት እና በጠበቀ የፋይናንስ ሁኔታ በሚታወቀው ዓለም አቀፋዊ አካባቢ ውስጥ አሁንም ስጋቶች ከፍተኛ መሆናቸውን ኮሚቴው አምኗል።
ወደፊት ስለሚወሰዱ እርምጃዎች ኮሚቴው በመግለጫው በሰጠው አቅጣጫ መሰረት፤ ቀጣዩ የፖሊሲ ስብሰባ በመጋቢት ወር 2018 ዓ.ም. እንዲካሄድ ተይዟል። ትክክለኛው ቀን ባይወሰንም፣ ስብሰባው በወሩ መጀመሪያ ላይ ወይም እንዳስፈላጊነቱ ቀደም ብሎ ሊካሄድ እንደሚችል ኮሚቴው ጠቁሟል።
ለጊዜው ማዕከላዊ ባንኩ የዋጋ ግሽበትን፣ የገንዘብ ዝውውርን፣ የብድር ዕድገትን እና የውጭ ኢኮኖሚያዊ ለውጦችን በቅርበት መከታተሉን እንደሚቀጥል አስታውቋል። የጠበቀ የገንዘብ ፖሊሲ በአጭር ጊዜ ውስጥ በብድር አቅርቦት ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር ቢችልም፣ የዋጋ መረጋጋትን መልሶ ማምጣት የባንኩ ዋነኛ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው፤ ይህ ግብ ደግሞ የሕዝቡን የመግዛት አቅም ለመጠበቅ እና ዘላቂ ዕድገትን ለመደገፍ ወሳኝ እንደሆነ ባንኩ ያምናል።
ፌስቡክ፡ https://web.facebook.com/addisreporternews/
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/addisreporter
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393






