በኦሮሞ ፌደራሊስ ኮንግረንስ አመራሮችና በጃዋር መሐመድ መካከል የፖለቲካ ሳይሆን የጥቅም ትስስር እንዳለ የሚያመልክቱ መረጃዎች እየወጡ ነው። አቶ በቅለ ገርባና ጃዋር መሐመድ የተጣሉትም በገንዘብ እንደሆነ ተመለከተ። ፓርቲው ጃዋርን ያስገባበትና ያስተናገደበት መንገድ አድሮ ጣጣ እንዳመጣም ተጠቁሟል።
ኦነግን ለመቀላቀል ጠይቆ “አይሆንም” የተባለው ጃዋር መሐመድ ፕሮርፌሰር መረራ የሚመሩትን ኦፌኮን የተቀላቀለበት አግባብ ፓርቲውን ዋጋ እንዳስከፈለው ያመለከቱ እንዳሉት፣ ጃዋር በፖለቲካ ትግልና በሚዲያ ስም ከሰበሰበው በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ውስጥ ለፓርቲው ምንም አልሰጠም። ይልቁኑም ለውስን አመራሮች በተለያዩ ጊዜያት ክፍያ ይፈጽም እንደነበር ተጠቁሟል።
“ጃዋር ድምጽ ስለሚቀርጽና፣ ገንዘብ ሲያስተላለፍ ሰነድ ስለሚይዝ የሁሉንም አፍ አዘግቷል” የሚሉት ወገኖች፣ ይህ ባይሆን ኖሮ የኦሮሞን ሕዝብ ተደራጅተው ለማጥፋት በይፋ ከሚዝቱ አደረጃጀቶች ጋር አብሮ ሲሰራ በፓርቲው ሕኛ ደንብ መሰረት ያግዱት ነበር።
“ጋላን እናጠፋለን፤ የጋላን መንግስት ከአራት ኪሎ እንነቅላለን፣ ወለጋን እንወስዳለን…” ከሚሉ ነፍጥ ያነሱ አካላት ጋር ጃዋር በገሃድ ሲሰራ፣ “አንተ የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር ነህ። የድርጅታችን መርህ ከትጥቅ ጋር ከሚሰሩ ኃይሎች ጋር አይሰራም” በሚል አስቸኳይ ስብሰባ ተጠርቶ ሊባረር ይገባው እንደነበር ያመለከቱት ድርጅቱን የለቀቁና በውስጥ ያሉ የኦፌኮ አመራሮች፣ “ይህ ያልሆነውና ይልቁኑም የሚከራከሩለት በጥቅም ስለያዛቸውና ስለገዛቸው ነው” ብለዋል።
እነዚሁ ወገኖች እንዳሉት የአቶ በቀለ ገርባና የጃዋር ጸብም መነሻው ገንዘብ እንደሆነ ጠቁመዋል። እስር ቤት እያሉ በስማቸው የተሰብሰበ ገንዘብ ወደ ጃዋር ሂሳብ መግባቱ፣ ከተፈቱ በሁዋላ በአውሮፓ በነበረ የምስጋና ጉዞ የተሰበሰበ ገንዘብ አሁንም በጃዋር አካውንት እንዲገባ መደረጉ አቶ በቅለን ውሎ አድሮ አስቆጥቷል።
አብረው በሄዱበት ለጊዜያዊ አገልግሎት የሚሆን አበል ንቢጤ እየተሰጣቸው የአውሮፓን ጉዞ ጨርሰው አሜሪካ አብረው ያቀኑት አቶ በቀለ አሜሪካ ሁለት የምስጋና ፕሮግራም ካካሄዱ በሁዋላ “ድርሻዬን አምጣ” ሲሉ ጃዋር በማፈግፈጉ ጥለውት እንደሄዱ ምስክሮችን ጠቅሰው ዜናውን ያቀበሉን አመልክተዋል።
ወደ አዲስ አበባ ሲገባ ግማሽ ቢሊዮን ብር ሰብስቦ የነበረው ጃዋር በተመሳሳይ በኦ.ኤም.ኤን ምስረታ አብረውት ሲሰሩ የነበሩትን በሙሉ “ዞር በሉ” እንዳላቸው ከወቅቱ ባልደረቦቹ መገለጹ ይታወሳል። አዲስ አበባ ከገባ በሁዋላ በአሜሪካ አብረውት ፕሮግራም ሲሰሩ የነበሩትን ባልደረቦቹን በማባረሩ እነ ዶክተር ኤታና፣ ጸጋዬ አራርሳ፣ መሀመድ አዴሞ ወዘተ በገሃድ ሚስጥሩን አውጥተው ሲዘልፉት እንደነበር አይዘነጋም።
አቶ በቀለ ገርባ “ለስከኮን ይክደኛል ብዬ አስቤ አላውቅም” በሚል ለሚቀርቡት ሰው ከመናገራቸው በቀር አደባባይ ወጥተው የተነፈሱት ነገር የለም። አቶ በቀለ ከወንጌል ጋር ያላቸው ቁርኝት ዝም እንዳሰናቸው የሚገልጹ ወገኖች ዳግም በሲያትሉና በቅርቡ በሜኖሶታ በተካሄደው የኦእሮሞ ልሂቃን ስብሰባ ከጃዋር ጋር መታየታቸው እንግዳ እንደሆነባቸው አመልክተዋል።
አልጸጸትም በሚለው የጃዋር መጽሐፍብ ላይ ❝…በዚህ ሁኔታ ለሦስት ቀናት በትንሽ በትንሹ ሾርባ እየወሰድን ሰውነታችንን ካለማመድን በኋለ በአራተኛው ቀን የምትፈልጉትን ምግብ እዘዙ ተባልን። እኔ ፓስታ አዘዝኩ፣ በቀለ ክክ ስላዘዘ «ያ ትላንቱ የአስተማሪነት ዘመን ድሀነት ናፈቀሀ እንዴ?››ብለን አሾፍንበት። ከሰዓት በኋላ የበቀለ ክክ ወጥ ጣጣ አመጣ።ከቀናት በፊት እንደሳቀብኝ እሱንም ተራው ደረሰው።በሆድ ቁርጠት ጀምሮት፣ ቀስ በቀሰ ተባብሶ ከላይ እና ከታች ያራውጡው ገባ። ራሱን ሲስት በጣም ተደናገጥን፡ የሚሞት መሰለን። ሐኪሞቹ ምን ማድረግ እንዳለባቸው።ፕሮፌሰር ከበደን ጠይቀው የነገራቸውን መድኃኒት ሲወጉት እንቅልፍ ይዞት ሄደ።ከአንድ ሰዓት በኋላ ሲነቃ «ሞቼ የገነት በር ላይ ሲደርስ ‘ጀዋርን ለምን ትተኸው መጣህ?!’ ብለው መለሱኝ ብሎ አሳቀን።❞ አልፀፀትም፤ጃዋር መሃመድ፤ገፅ 374/ በማለት የሁለቱን ግንኙነት እስከ ቀራኒዮ የሚጸና አስመስሎ ያቀረበው ጃዋር መሐመድ ከብር እና ከብር ጋር በተያያዙ ወንጀሎች ስም በከፍተኛ ደረጃ የሚነሳ “ለኦሮም ሕዝብ ተቆርቋሪ ነኝ” የሚል አክቲቪስት ነው።
ይህ በንዲህ እንዳለ ጃዋር መሐመድ ከዚህ ቀደም ያልተሳካውን የሽምግልና ጥያቄ ማቅረቡ ተሰምቷል። ጃዋር “አሸማግሉኝ” በማለት ጥሪ ያቀረበርው በሚቀርባቸው ሽማግሌዎች ሲሆን፣ በፍርድ ቤት የታገደበት ሃብት ከተመለሰለት ዝም እንደሚል መግለጹ ታውቋል። ዜናውን የነገሩን እንዳሉት አሁን ላይ ጃዋር በኦሮሚያ የተረሳና በሕዝብ፣ በፖለቲካ ድርጅቶች እንዲሁም ጫካ ባሉ አካላት ሳይቀር ሲሰጠው የነበረው ልዩ ትኩረት በመትነኑ ጥሪው የደረሳቸው የመንግስት አካላት ለጊዜው ብዙም ትኩረት እንዳልሰጡት ጠቁመዋል። ምክንያታቸው ደግሞ “አይታመንም” የሚል ነው።
ጃዋርም ሆነ አቶ በቀለ ይህን ጉዳይ አስመልክቶ ምላሽ እንዲሰጡ በተደጋጋሚ በእጅ ስላካቸው ሙከራ ቢደረግም ጥሪውን በመመለስ አልተባበሩም።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter11
X፡ https://x.com/addisreporter
ፌስቡክ፡ https://www.facebook.com/profile.php?id=61577410241403
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393






