አዲስ ሪፖርተር – የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በቅርቡ የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ኢራን ለምን ለፍላጎታቸው ተገዥ እንዳልሆነች እንደጠየቋቸው መናገራቸውን ተከትሎ በሰጡት ምላሽ “እኛ ኢራናዊ ስለሆንን” ነው ሲሉ ምላሽ ሰጡ።
አራጋቺ እሁድ ዕለት ኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት ዊትኮፍ “ኢራን ለዋሺንግተን ፍላጎቶች ለምን እንዳልተገዛች ተጠይቀው ነበር። “ምክንያቱም ኢራናውያን ስለሆንን ነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
የአሜሪካ ዋነኛ ተደራዳሪ የሆኑት ልዩ መልዕክተኛው ስቲፍቭ ዊትኮፍ ከፎክስ ኒውስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልስ ወቅት ትራምፕ ኢራን ይህ ሁሉ ጫና እየተደረገባት አልበገርም ለምን እንዳለች ማወቅ እንደሚፈልጉ ገልጸው ነበር። ልዩ መልዕክተኛው አሜሪካ በቀጣናው የጦር ጄት ተሸካሚ መርከቧን ብታሰማራም “እጇን ያልሰጠችው” ለምን እንደሆነ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ማወቅ ይፈልጋሉ ብለዋል።
“ዛሬ ጠዋት ፕሬዚዳንቱ ጠይቀውኛል። ተስፋ ቆርጠዋል ማለት አልፈልግም። ምክንያቱም ብዙ አማራጮች እንዳሏቸው ያውቃሉ። ነገር ግን ለምን እጃቸውን እንዳልሰጡ፤ እንዳልተስማሙ ማወቅ ይፈልጋሉ።” ዊትኮፍ እንደሚሉት የትራምፕ አስተዳደር ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንደማትታጠቅ እና ያንን ለማረጋገጥ ተጨባጭ እርምጃዎችን እንድትዘረዝር ይፈልጋል።
ይህ አስተያየት የመጣው ሁለቱ አገራት ለሦስተኛ ዙር ውይይት ከመገናኘታቸው በፊት ነው። ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ በኦማን አደራዳሪነት ሁለቱ አገራት በስዊዘርላንድ ጄኔቫ ተገናኝተው ተወያይተዋል። አሜሪካ ጦር ጫኝ መርከቦቿን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ማንቀሳቀሷን ተከትሎ ጥቃቶቸ ሊፈጸሙ እንደሚችሉ ተገልጾ ነበር። እሁድ ዕለት በተለያዩ የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎቸ የሚማሩ ኢራናውያን ለተቃውሞ አደባባይ ወጥተው ነበር።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addisreporternews
ስልክ ቁጥር፡ +251116393393






