የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ የፌዴራል መንግሥት ለትግራይ ክልል ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና የሕዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያለውን ጽኑ አቋም በግልጽ ያሳየ ነው – ስምረት ፓርቲ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በትግራይ ክልል ጉዳይ የሰጡት ማብራሪያ የፌዴራል መንግሥት ለክልሉ ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና የሕዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያለውን ጽኑ አቋም በግልጽ ያሳየ መሆኑን ስምረት ፓርቲ አስታወቀ።
የቀድሞ ሕወሓት ቡድን ወጣቱን ለዘመናት ተብትቦ ያቆየበት የተሳሳተ አመለካከት የተሰበረበትና እንደማያዋጣ ያስገነዘቡበት መሆኑ በክልሉ ተራማጅ ወጣቶችን ለመፍጠር ትልቅ እድል እንደሚሰጥ ተገልጿል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በትግርኛ ቋንቋ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የትግራይ ሕዝብ ከጦርነት ይልቅ ሰላምና ልማት ይገባዋል ብለዋል። መንግሥት በትግራይ ክልል ሰላም እንዲሰፍንና ዳግም ጦርነት እንዳይከሰት ጽኑ ፍላጎት እንዳለውና ለዚህም ማንኛውንም መስዋዕትነት እንደሚከፈል አብራርተዋል።
ወጣቶች የስልጣን ባለቤት እንዲሆኑና በአሮጌ አስተሳሰብ ለጦርነት ከሚገፋፏቸው አካላት ራሳቸውን እንዲጠብቁም አሳስበዋል። በፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት መሰረትም መንግሥት የባንክ፣ የኤሌትሪክ ኃይልና ቴሌኮም የመሳሰሉ አገልግሎቶችን በፍጥነት እንዲመለሱ ማድረጉን አስታውሰዋል።
ይህን ተከትሎ የስምረት ፓርቲ ምክር ቤት አባልና የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ክፍል ኃላፊ ጣዕመ አርዓዶም ከኢዜአ ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ማብራሪያ የሀገሪቷን ብሎም የትግራይ ክልልን ነባራዊና አሁናዊ ሁኔታን በግልጽ ያስቀመጠ ነው። ለትግራይ ክልል ልማትና ዕድገት ሰላምና መረጋጋት ወሳኝ ስለመሆኑ ጠንካራ መልዕክት የተላለፈበት ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በትግርኛ ቋንቋ የሰጡት ማብራሪያ የትግራይን ሕዝብ ያከበረ፣ ለሰላምና መረጋጋት ቅድሚያ በመስጠት ግልጽ መልዕክት ያስተላለፈ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ለሕዝቡ ትልቅ እፎይታን የሚያጎናጽፍና ለዘላቂ ሁለንተናዊ እድገት ወሳኝ እንደሆነ ተናግረዋል። የክልሉ ሕዝብ ሲያነሳው ለቆየው የሰላም፣ የልማትና የእድገት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ መሆኑንም ነው ያመለከቱት። በተጨማሪም በትግራይ ክልል ብቻ ሳይሆን በኤርትራ በኩል የጽንፈኛው የሻዕቢያ ቡድን ሴራን በትክክለኛ መረጃ ላይ በመመስረት ያጋለጠ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ሕዝቡን መጠቀሚያ በማድረግ የራሳቸውን ሴራና እኩይ ተግባር ለመፈጸም እየሠሩ ላሉ ሕገ ወጥ ቡድኖች ትልቅ መልዕክት የተላለፈበት ነው ያሉት ኃላፊው፤ ለሕዝቡ ሲባል መንግሥት ያሳየው ታጋሽነት ከፍተኛ መሆኑን ያመላከተ ነው ብለዋል። ይህም በትግራይ ሕዝብና በቀድሞ ሕወሓ ቡድን መካከል ሰፊ ልዩነት እንዳለ ጠቅሰው፤ መንግሥት ይህንን ባገናዘበ መልኩ ለሕዝብ ያለውን ወገንተኝነት በግልጽ ማሳየቱን ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወጣቶች የስልጣን ባለቤት እንዲሆኑና በአሮጌ አስተሳሰብ ለጦርነት ከሚገፋፏቸው አካላት ራሳቸውን እንዲጠብቁ የሰጡትን ምክረ ሐሳብ ጠንካራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ክልሉ ለወጣቶች በባለቤትነት የተሰጠ በመሆኑ ትልቅ መነቃቃትን እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
የቀድሞ ሕወሓት ቡድን ወጣቱን ለዘመናት ተብትቦ ያቆየበት የተሳሳተ አመለካከት የተሰበረበትና እንደማያዋጣም ያስገነዘቡበት መሆኑን ጠቅሰው፤ በክልሉ ተራማጅ ወጣት ለመፍጠር ትልቅ ዕድል እንደሚሰጥ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት የትግራይ ወጣት ከቀድሞ ሕወሓት ቡድን ጋር የመሰለፍ ምንም ዓይነት ፍላጎት እንደሌለው በተለያዩ ሁኔታዎች እያሳየ መሆኑ ገልጸው፤ ወጣቱ ለአሮጌ አስተሳሰብ ራሱን አሳልፎ መስጠት እንደማይፈልግ አቋም አለው ነው ያሉት።
የፌዴራል መንግሥት ለትግራይ ክልል ለልማት የመደበውን በጀት የቀድሞ ሕወሓት ቡድን ለጦርነት ዝግጅትና ለታጣቂዎች ቀለብ እያዋለ መሆኑን በግልጽ የተነተኑበት መንገድ የቡድኑን እኩይ ተግባር ያጋለጠ እውነታውን ያረጋገጠ ነው ብለዋል።
የትግራይ ክልልን ጸጥታ በማደፍረስ ሥራ ላይ የተጠመደው የቀድሞ ሕወሓት ቡድን ለሕዝብ ጥቅም እና ልማት የሚመደብ በጀትን ለግል ጥቅማቸው በማዋል ሕዝቡን ለተባባሰ ችግርና መከራ ዳርጎታል ብለዋል።
በተጨማሪም በክልሉ የመንግሥት ሠራተኞች ያለፍላጎታቸው ከደመወዛቸው ገንዘብ እየተቆረጠ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህም ሕዝቡን ተስፋ በማስቆረጥ ክልሉን ወደ ጦርነት ለማስገባት የሚደረግ ጥረት ማሳያ ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ያስተላለፉት መልዕክት ለትግራይ ሕዝብ እጅግ ወቅታዊና ተጠባቂ ከመሆኑ ባሻገር ለክልሉ ሕዝብ ትልቅ እፎይታና እረፍት የሚሰጥ መሆኑን ነው የገለጹት። ከቀድሞ ሕወሓት ቡድን ለመላቀቅ ጽኑ ፍላጎት ላለው የትግራይ ሕዝብ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ ተስፋ የሚሰጥና ፊቱን ወደ ልማትና ብልፅግና እንዲያዞር እድል የሚፈጥር መሆኑንም አብራርተዋል።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addisreporternews
ስልክ ቁጥር፡ +251116393393






