አዲስ ሪፖርተር – የወልቃይት ጠገዴ አማራ የማንነት እና ወሰን አስመላሽ ኮሚቴ፣ በኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ እና በዲሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ (ስምረት) መካከል በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት እየተካሄደ ባለው የሕግ ክርክር ውስጥ፣ “መብትና ጥቅሜን ይነካል” በማለት የጣልቃ ገብነት አቤቱታ አቅርቧል።
ፍርድ ቤቱ የኮሚቴውን አቤቱታ መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለየካቲት 25 ቀን 2018 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል።
ክርክሩ የተጀመረው የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የካቲት 16 ቀን 2018 ዓ.ም. በአማራ እና በትግራይ ክልሎች መካከል አከራካሪ በሚባሉ የምርጫ ክልሎች ላይ በሰጠው ውሳኔ ላይ ተመስርቶ ነው። ቦርዱ የሰጠውን ውሳኔ በመቃወም የዲሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ ፓርቲ ባቀረበው የእግድ አቤቱታ መነሻነት፣ ፍርድ ቤቱ የቦርዱ ውሳኔ ለጊዜው ታግዶ እንዲቆይ ትዕዛዝ መስጠቱ ይታወሳል።
የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት እና ወሰን አስመላሽ ኮሚቴ በጠበቃው ቴዎድሮስ ታደሰ አማካኝነት ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው አቤቱታ፣ በጉዳዩ ላይ ጣልቃ መግባት ያስፈለገበትን ዋና ዋና ነጥቦች ዘርዝሯል።
የሁመራ እና የአድረመፅ የምርጫ ክልሎች ከ2013 ዓ.ም. ጀምሮ ከትግራይ ክልል ወጥተው በወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን ስር ራሳቸውን እያስተዳደሩ መሆናቸውን ገልጿል።
ኮሚቴው ላለፉት አሥር ዓመታት የሕዝብ ፒቲሽን (ፊርማ) በማሰባሰብ የሕዝቡን የማንነትና የወሰን ጥያቄ በሕጋዊ ውክልና ሲያስፈጽም የቆየ አካል መሆኑን ጠቅሷል።
በኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ሕገ-መንግሥት አንቀፅ 38 የተደነገገው የመምረጥና የመመረጥ መብት በቀጥታ የሚነካ በመሆኑ፣ ኮሚቴው ባልተሳተፈበት የፍርድ ቤት ክርክር የሚሰጥ ማንኛውም ውሳኔ በሕዝቡ ላይ የጥቅም ጉዳት እንደሚያደርስ አመልክቷል።
ኮሚቴው በፍታብሔር ሥነ-ሥርዓት ሕግ ቁጥር 41 መሠረት በክርክሩ ውስጥ ገብቶ እንዲከራከር እንዲፈቀድለት የጠየቀ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱም ይህንኑ የጣልቃ ገብነት ጥያቄ መርምሮ ብይን ለመስጠት ለየካቲት 25 ቀን ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
ይህ ክርክር አከራካሪ በሆኑት አካባቢዎች የሚካሄደውን ምርጫ እና የወደፊት የአስተዳደር መዋቅርን አስመልክቶ የሚሰጡ ውሳኔዎች ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ይኖረዋል ተብሎ ይጠበቃል።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addisreporternews
ስልክ ቁጥር፡ +251116393393






