አዲስ ሪፖርተር – ፎርብስ አፍሪካ መፅሔት በአፍሪካ እድገት ላይ የሚያተኩር ሪፖርቶችን በየዓመቱ በማውጣት የሚታወቅ መፅሔት ሲኾን መፅሔቱን እንደ ትልቁ “አህጉራዊ መድረክ” ይቆጠራል። በዚሁ መፅሔት ላይ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን ኩባንያዎች በተለያዩ ዘርፎች እያስመዘገቡት ያለውን እድገት ከፍተኛ መኾኑን ገልጾ የፊት ገፁ ላይ ይዞ አግኗቸዋል።
መፅሔቱ፣ ኢትዮጵያ እየተጓዘችበት ያለውን የእድገት ጎዳና የሚያትትና ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ የሚገኙትን በፊት ለፊት ገፁ ይዞ የወጣ ሲኾን የመንግስት ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ ያሉ ምጣኔ ሐብት አከናዋኞችን ያካተተ ዘገባ አስነብቧል።
በዘገባው፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ ፕሬዝዳንት ታዮ አፅቀ ስላሴ፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ፣ የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ ብሩክ ታዮ እንዲሁም የቀድሞ የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴን መፅሔቱ የ2025 ተፅእኖ ፈጣሪዎች ከቀዳሚዎቹ ተርታ አሰልፏቸዋል።
ከግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ ደግሞ የቀርጨንሼ ግሩፕ ባለቤትና ስራ አስፈጻሚ እስራኤል ደገፋ፣ ሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ ጀማል አሕመድ፣ የኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ ሊቀመንበር ብዙአየሁ ታደለ እና የሰንሻይን ኢንቨስትመንት ግሩፕ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ተስፋዮን ተፅዕኖ ፈጣሪ የቢዝነስ ሰዎች በሚል ሪፖርቱ አካቷል።
ኢትዮጵያ እየተጓዘችበት ያለውን የእድገት ጎዳና የሚያስመሰግን መኾኑን የገለፀው ይኸው መፅሔት በተለያዩ ዘርፎች ያካተተ ሲሆን በግብርና፣ ኮንስትራክሽን፣ የሆቴል ዘርፍ እንዲሁም በኢንዱስትሪ የቢዝነስ ከባቢዎች ይበል የጎላ አስተዋፅኦ ያላቸው አካላት መሆናቸውን ከፎርብስ አፍሪካ መፅሔት ተመልክተናል ።
በተለይም መፅሔቱ ተለዋዋጭ በሆኑ እድገቶች ላይ ትኩረት የሚያደርግ ሲኾን በየዓመቱ የተመረጡና የሚጨበጥ ለውጥ ያመጡ አፍሪካውያንን በፊት ገፁ ይዞ በመውጣት ይታወቃል።
በዚሁ 2025 የፎርብስ አፍሪካ እትም ከኢትዮጵያ የተወከሉ ተቋማትና ሰዎች ከሌሎች ዓመታት ጋር ሲነጻጸር የዘንድሮው በርካታ ሆኖ ታይቷል።
መፅሔቱ ጥልቅ ዳሰሳ ካደረገባቸው ስድስት ተፅእኖ ፈጣሪ ኩባንያዎች መካከል “ቀርጨንሼ ቢዝነስ ግሩፕ” አንዱ ሲኾን የቡና አመራረት ዘዴን በመቀየር የሚታወቅ። እንደ ሆቴል፣ የቀለምና ብረታብረት ፋብሪካ እንዲሁም በአውቶሞቲቪ በመሳሰሉት ዘርፎችየተሰማራ ኩባንያ ነው።
ፎርብስ አፍሪካ መፅሔት አንጋፋውን ሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕንም ጠቅሷል። ኩባያው በማዕድን፣ በሆቴል፣ በግብርና፣ በሲሚንቶና በተለያዩ ምርቶችና አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ኢትዮጵያ ውስጥ ፊት መሪ መሆኑ ይታወቃል። ሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በጥቅሉ ከ40 በላይ ድርጅቶችን ያስተዳድራል።
“ሰንሻይን ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ” የቤት አቅቦትና ከ35 አመታት በላይ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ልምድ ያለው ኩባንያ ነው። በራስ አቅም ወደ ኢንቨስትመንት ያደገ መኾኑንና በስሩ በርካታ የስራ እድሎችን በመፍጠር የግንባታ ዘርፍ አስተዋፅኦ አድርጓል ሲል መፅሔቱ መርጦታል።
ሌላኛው በፎርብስ አፍሪካ መፅሔት ከተካተቱት ኢትዮጵያዊያን ድርጅቶች መካከል ሌላኛው ከፍተኛ ለውጥ ያመጣው “ኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ” ኩባንያ ሲኾን በተለዋጭ ኢነርጂ፣ በግብርና፣ ሪልስቴት፣ ማእድን እንዲሁም በሎጂስቲክስ ዘርፎች እድገት ላይ ከፍተኛ ሚና የተጫወተ ኩባንያ በማለት ጠቅሶታል





