ዶላር መያዝ ወይስ ወርቅ? የአሜሪካው ፖለቲካ ያስከተለው ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ውዝግብ

Date:

አዲስ ሪፖርተር – በትላንትናው እለት በአሜሪካ የተሰማ ያልተጠበቀ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ክስተት ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ገበያዎችን አናግቷል። ይህ የተሰማው የአሜሪካ የፍትህ ሚኒስቴር በፌዴራል ሪዘርቭ (የአሜሪካ ማዕከላዊ ባንክ) ሊቀመንበር ጄሮም ፓውል ላይ የወንጀል ምርመራ መጀመሩን ማስታወቁን ተከትሎ ነው።

ምርመራው ትኩረት ያደረገው ፓውል በፌዴራል ሪዘርቭ ዋና መስሪያ ቤት ስለተከናወነ ከፍተኛ ወጪ የጠየቀ የእድሳት ፕሮጀክት ለኮንግረስ በሰጡት መግለጫ ላይ ነው።

ሮይተርስ እና ፋይናንሺያል ታይምስ እንደዘገቡት፣ ፓውል “አጥፍተዋል” የተባሉትን ማንኛውንም ዓይነት ውንጀላ አጥብቀው ያስተባበሉ ሲሆን፣ ምርመራው የዓለምን ኢኮኖሚ በማረጋጋት ረገድ ቁልፍ ሚና የሚጫወተውን የፌዴራል ሪዘርቭን ነፃነት ሊያሳጣ ይችላል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

የምርመራው ዜና ጥር 05 ቀን እንደተሰማ በፍጥነት የባለሃብቶች መተማመን እንደቀነሰ ተስምቷል። ስለተፈጠረው ሁኔታ የፋይናንስ ገበያዎች በጥንቃቄ እና በጭንቀት ምላሽ ሰጥተዋል።

በፌዴራል ሪዘርቭ ላይ የተፈጠረው አለመረጋጋት የወደፊት የወለድ ተመን ውሳኔዎችን ሊጎዳ ይችላል በሚል ስጋት ዋና ዋና የአሜሪካ የአክሲዮን ገበያዎች ቀንሰዋል።

በተመሳሳይ ጊዜ የአሜሪካ ዶላር ከሌሎች ዋና ዋና ገንዘቦች አንጻር ዋጋው ወርዷል። የዶላር ጥንካሬ በብዛት የተመሰረተው በአሜሪካ ተቋማት ላይ ባለው ዕምነት ሲሆን፣ ያ እምነት ሲናጋ ዓለም አቀፍ ባለሀብቶች በዶላር ላይ የተመሰረቱ ሀብቶቻቸውን ይቀንሳሉ።

የውጭ ምንዛሪ ገበያዎች የታየው ከፍተኛ እንቅስቃሴ የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት በአሜሪካ የኢኮኖሚ መሪነት ላይ ያለውን የረጅም ጊዜ እምነት ሊያዳክም ይችላል የሚል ስጋትን ያንፀባርቃል።

ዶላር ዋጋው እየቀነሰ በሄደበት ወቅት ወርቅ በተቃራኒው አቅጣጫ ተጉዟል። ባለሀብቶች እርግጠኛ ባልሆኑ ጊዜያት ሀብታቸውን ለማስቀመጥ አስተማማኝ  አድርገው ወደሚቆጥሩት ወርቅ ፊታቸውን አዙረዋል። ፋይናንሺያል ታይምስ እንደዘገበው፣ ገንዘብ ከሌሎች ምንዛሬዎች እና ስጋት ካለባቸው ንብረቶች ወጥቶ ወርቅ ላይ በመፍሰሱ የወርቅ ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ ንሯል።

ይህ ለውጥ ባለሀብቶች ለአንድ ምርመራ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ለዓለም አቀፍ የፋይናንስ መረጋጋት ስጋት ምላሽ እየሰጡ መሆናቸውን ያሳያል። የቦንድ ገበያዎችም ይህንኑ ጭንቀት አንፀባርቀዋል፤ ነጋዴዎች የፖለቲካ ውጥረቱ ከቀጠለ በአሜሪካ የገንዘብ ፖሊሲ ላይ ለውጦች ሊመጡ እንደሚችሉ መጠበቅ ጀምረዋል።

እነዚህ ክስተቶች ከኢትዮጵያ ርቀው ቢፈጠሩም ተጽኖአቸው ግን በአሜሪካ ወይም በአውሮፓ ብቻ የተገደበ አይደለም። ኢትዮጵያ እንደማንኛውም አገር በንግድ፣ በምንዛሪ ገበያ እና በኢንቨስትመንት አማካኝነት ከዓለም አቀፉ የፋይናንስ ስርዓት ጋር የተገናኘች ናት። በአሜሪካ ዶላር ዋጋ ላይ የሚመጡ ለውጦች የገቢ ዕቃዎች ወጪን፣ የዋጋ ግሽበትን እና የውጭ ምንዛሪ አቅርቦትን ሊነኩ ይችላሉ።

የዶላር መዳከም እንደ ነዳጅ፣ ማሽነሪ ወይም መድኃኒት ያሉ የገቢ ዕቃዎችን ዋጋ ሊቀንስ ይችላል ምክንያቱም ተመሳሳይ መጠን ያለው ዶላር ለመግዛት ጥቂት ብር ብቻ ሊፈጅ ይችላል። ሆኖም ግን ዓለም አቀፋዊ አለመረጋጋት የውጭ ኢንቨስትመንትን ሊቀንስ እና ዓለም አቀፍ ብድር ወይም ፋይናንስ የማግኘት እድልን አስቸጋሪ ሊያደርገው ይችላል።

ይህ ሁኔታ በኢትዮጵያ ውስጥ ልዩ ትኩረት የሚሻ ነው፤ ብዙ ግለሰቦች ቁጠባቸውን ብርን ወደ አሜሪካ ዶላር በመቀየር ከባንክ ውጭ በድብቅ ያስቀምጣሉ።

 የፍትህ ሚኒስቴሩ ምርመራውን ካወጀበት ቀን በኋላ እንደታየው ዶላር ራሱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዋጋው ሲቀንስ፣ በድብቅ የተያዙት ዶላሮች የመግዛት አቅማቸውም ሊቀንስ ይችላል።

ይህም ማለት ብራቸውን ወደ ዶላር ቀይረው ያስቀመጡ ሰዎች፣ በተለይም ዋጋው በከፍተኛ ሁኔታ ከጨመረው እንደ ወርቅ ካሉ ንብረቶች ጋር ሲነጻጸር፣ ሀብታቸው ሊቀንስ ይችላል ማለት ነው።

ይህ ዓይነቱ ድርጊት በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይም ሰፊ መዘዝ አለው። ከፍተኛ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሪ ከባንክ ውጭ ሲቀመጥ፣ ያ ዶላር ለኦፊሴላዊ ንግድ፣ ለገቢ ዕቃዎች ወይም ለምርታማ ኢንቨስትመንት አይውልም። ይህም የውጭ ምንዛሪ አቅርቦትን በመቀነስ በብር ላይ ተጨማሪ ጫና ይፈጥራል፤ እንዲሁም የኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ወደ ህገ-ወጥ ገበያ እንዲያመራ ያደርጋል።

በጊዜ ሂደት ይህ ለከፍተኛ የሸቀጦች ዋጋ እና ለዋጋ ግሽበት አስተዋፅኦ ያደርጋል፤ ይህም በህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር የማይሳተፉትን ጨምሮ እያንዳንዱን ዜጋ ይጎዳል። እንደ አሁኑ ያለ ዓለም አቀፍ አለመረጋጋት ባለበት ወቅት፣ የውጭ ምንዛሪን በግል መያዝ እንደ ጥበቃ ሊታይ ይችላል፤ ነገር ግን ለግለሰቡም ሆነ ለአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ውጥረትን ይጨምራል።

የዓለም አቀፍ የወርቅ ዋጋ መጨመርም ለኢትዮጵያ ድብልቅ ትርጉም አለው። በአንድ በኩል ኢትዮጵያ ወርቅ አምራች በመሆኗ፣ ከፍተኛ ዋጋ ለላኪዎች ጥቅም የሚሰጥና ተጨማሪ የውጭ ምንዛሪ የሚያስገኝ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ፣ የወርቅ ዋጋ መጨመር ብዙውን ጊዜ በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ያለውን ፍርሃትና አለመረጋጋት ያሳያል።

እንዲህ ያሉ ሁኔታዎች ዓለም አቀፍ ባለሀብቶች እንደ ኢትዮጵያ ባሉ በማደግ ላይ ባሉ ኢኮኖሚዎች ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ስለሚያደርግ፣ የኢንቨስትመንት ፍሰትንና የሥራ ዕድል ፈጠራን ሊያቀዘቅዝ ይችላል። ለዜጎችም ቢሆን፣ ሀብትን በጥሬ ገንዘብ (በብርም ይሁን በዶላር) መያዝ፣ የዓለም ገበያ ሲለዋወጥ የራሱ የሆነ አደጋ እንዳለው የሚያሳይ ነው።

Photo Credit: REUTERS

ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393

Share and Enjoy !

Shares

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

Share post:

Subscribe

spot_imgspot_img

Popular

More like this
Related

በፀረ-ሽብርተኝነት እና በመፈራረስ መካከል ያለቸው ሶማሊያ “ሌላ አፍጋኒስታን?” የአሜሪካና አቋምና የአል-ሸባብ….

አዲስ ሪፖርተር - እ.ኤ.አ. ነሐሴ 2021 ዓለምን ያስገረመው የአፍጋኒስታን...

የኢትዮጵያ፣ ህንድ እና እስራኤል ስትራቴጂካዊ አጋርነት የቀጠናው ፖለቲካዊ ትኩሳት፤ የኤርትራ መጨማደድ

አዲስ ሪፖርተር - ባለፈው ማክሰኞ በኢየሩሳሌም የተካሄደው የህንድ እና...

ጀርመንና ሕንድ ግንኙነታቸውን ወደ ስትራቴጂክ አጋርነት አሳደጉ

አዲስ ሪፓርተር - የጀርመኑ መራሄ መንግሥት ፍሪድሪክ ሜርዝ በሕንድ...

መነሻውን ኤርትራ ያደረገ የጦር መሳሪያ ወልደያ ኬላ ላይ ተያዘ፤ መዳረሻው ሸዋ ሮቢት ነበር

አዲስ ሪፖርተር - መነሻውን ኤርትራ ያደረገ የጦር መሳሪያ ወልደያ...