ትህነግ ወታደራዊ ኃይሉን በፖለቲካ ብልጠት ለማስደገፍ እየተውተርተረ ነው! “ቆሞ ቀረ ነው አይሆንለትም”

Date:

አዲስ ሪፖርተር – የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር/ ትህነግ አሁን “እየተንፈራገጠ ነው” የሚሉ እየበዙ ነው። ትህነግ በትግራይ ውስጥ “ታቦት ነው” ሲሉ የነበሩ ጀርባቸውን ሰጥተውት ከትህነግ በሁዋላ በትግራይ ስለሚተከለው ፖለቲካ እየመከሩ ነው። የፌደራል መንግስትም ወደ ምርጫ እየሄደ በመሆኑ እያመረረ ነው። ሻዕቢያ ፋኖና ትህነግን ይዞ አዲስ “የሰሜን ህብረት መፍጠር” በሚል እየተወተረተር ነው። ይህ ሁሉ እየሆነ ቢሆንም ትህነግን ጠንቅቀው የሚያውቁ ትህነግ ጥይት እንደማይተኩስ ይናገራሉ። ለዚያ የሚያበቃ የሕዝብ ድጋፍ፣ የወታደሮች የውጊያ ሞራልና የፌደራል መንግስትን ዱላ የሚቋቋምበት የሎጅስቲክ ኃይል አይኖረውም።

ሰሞኑን ተፈናቃዮችን ስመልክቶ በተደጋጋሚ እየተነሳ ያለው ዘመቻ ትህነግ ያጣውን የሰራዊትና የሕዝብ ድጋፍ በቁጭትና በብስጭት ለማነሳሳት በማሰብ እንጂ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል እንዳልሆነ የትግራይና ከትግራይ ውጭ የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚ ኃይሎች “ቆመ ቀር” እያሉ በመግለጽ ላይ ናቸው። ጦረንቱን በሚዲያ ሲመሩ የነበሩ የትህነግ ታማኝ የሚዲያ ክንፎች መካከል የርዕዮት ሚዲያ ባለቤት ቴዎድሮስ “እነዚህ የርሃብ ጠማቂዎች” በማለት እብሯቸው ከሚቀርቡ ባልደረቦቹ ጋር በመሆን ትህነግን ለጆሮ በሚከብዱ ቃላቶች እያራገፋቸው ነው።

“ድንቁርና ድምጽ አውጥቶ ስልክ ቢደውል፣ የሚሰማው የትህነግ ድምጽ ነው” በማለት አስተሳሰባቸውን እየተጠየፈ፣ እየተገረመና፣ “እንዴት ሰው በዚህ ደረጃ ያስባል?” በሚል መገረም ትህነግን በትችት እየገረፈ ያለው ቴዎድሮስ፣ ከስህተታቸው አለመማራቸውን፣ ሊማሩ የማይችሉ መሆናቸውን በማመልከት እየነቀፈ ነው። በትግራይ ውስጥም ቢሆን ተቃወሞው ከተራ ነዋሪ ጀምሮ እስከ ሰራዊቱ ውስጥ ዘልቋል።

ትህነግ ይህን በደንብ እንደሚረዳ የሚናገሩ አሁን ያለው ግርግር የተገፈፈውን የትህነግን ዕውቅና ለማስመለስና በምርጫ እንደምንም ብሎ ለማሸነፍ፣ በዚያ ውስጥ ለዘረፈው፣ ለሰራው ወንጀልና በደል አምነስቲ እንዲሆነው ስልጣኑን ለማራዘም እንጂ ሌላ ፍላጎት ኖሮት እንዳልሆነ በርካቶች ይስማማሉ።

የውስጥ አዋቂ መረጃዎችን በሰፊ ትንታኔ በማቅረብ የሚታወቀው ዘ አፍሪካን ሪፖርት ራሱን ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ በተገንጣይ ስም ሰይሞ የሚነቀሳቀሰውን የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር / ትህነግን አስመልክቶ ከላይ በተባለው ደረጃም ባይሆን የራሱን እይታ አስቀምጧል። Ethiopia: Tigray People’s Liberation Front balancing act በሚል ርዕስ የቀረበውን ጽሁፍ የዝግጅት ክፍላችን እንዳለ አትሞታል።

ለኢትዮጵያ ሰላም ዋነኛው ስጋት የሆነው ወታደራዊ ኃይልን ከፖለቲካዊ ብልሃት ጋር ለማመጣጠን እየሞከረ ያለው የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር (ትህነግ) የሰላም ስምምነቱ የሲቪል አስተዳደርን ለመመለስ ያለመ ቢሆንም አሁንም ትግራይን በትጥቅ ኃይል እየተቆጣጠረ ይገኛል ይላል የ ዘ አፍሪካ ሪፖርት።

ሪፖርቱ አክሎ ትህነግ የፌዴራል ሕጎችን ይቃወማል፤ እንዲሁም ከአማፂ ቡድኖች ጋር አብሮ በመስራት ተጠያቂ ያደርገዋል። ስም ባይጠቅሰም ሪፖርቱ የመንግሥት ባለሥልጣናት ክልሉ አሁንም በፓርቲው ይፋዊ ባልሆነ ወታደራዊ ቁጥጥር ስር ባለበት ሁኔታ፣ ሕጋዊና ተዓማኒነት ያለው ምርጫ በትግራይ ለማካሄድ አስቸጋሪ እንደሚሆን መግለጻቸውን ይናገራል።

በቅርብ ጊዜ በኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ያለው ውጥረት እየተባባሰ መጥቷል፤ ይህም የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር (ትህነግ) ወደ ህጋዊ መስመር እንዲገባ ከፌዴራል መንግሥት የሚደርስበት ግፊት እየጨመረ በመምጣቱና ከባድ ውስጣዊ ፈተናዎች ስለገጠሙት ነው። ዘ አፍሪካ ሪፖርት እንደዘገበው ፓርቲው ቀደም ሲል የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር መሪ አቶ ጌታቸውን ከሥልጣን አንስቷል። ከቀድሞ ጠላቶቹ/ ሻዕቢያ ጋር ያለውን ግንኙነት እንደገና አድሷል። እንዲሁም ከአገራዊ ምርጫ በፊት ሕጋዊ ሰውነቱን አጥቷል። ይህ ሁኔታ ከኢኮኖሚ ችግርና በወታደሮች መካከል ካለው አለመረጋጋት ጋር ተዳምሮ የፖለቲካ ፍጥጫው በድጋሚ ወደ ግልጽ ጦርነት ሊቀየር ይችላል የሚል ሥጋት እንዲፈጠር አድርጓል።

ትህነግ ወደዚህ ደረጃ እንዴት ሊደርስ እንደቻለ ለመረዳት ያለፈ ታሪኩን መመልከት አስፈላጊ ነው። እ.ኤ.አ. በ1991 በኢትዮጵያ ሥልጣን ከያዘ በኋላ ትህነግ ለሦስት አስርት ዓመታት ያህል የአገሪቱን ፖለቲካ በበላይነት ተቆጣጥሯል። ይሁን እንጂ እ.ኤ.አ. በ2018 አብይ አህመድ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሆኑ በኋላ ይህ ሁኔታ ተለወጠ። ዘ አፍሪካ ሪፖርት የጠቀሳቸው የፖለቲካ ታዛቢዎች እንደሚሉት፤ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መንግሥትና በትህነግ መካከል ያለው ውጥረት በፍጥነት ተባባሰ። ይህ ውጥረት በመጨረሻ እ.ኤ.አ. በኖቬምበር 2020 ወደ አስከፊ ጦርነት ተቀየረ። በግጭቱ ወቅት የፌዴራል ኃይሎች በኤርትራ እና ፋኖ ተብለው በሚጠሩ የአማራ ታጣቂዎች በመታገዝ ትህነግን እና ወታደራዊ ክንፉን የትግራይ መከላከያ ኃይልን ዛሬ ላለበት ደረጃ አደረሱት።

እ.ኤ.አ. በ2022 መገባደጃ ላይ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት እስኪፈረም ድረስ ጦርነቱ ያስከፈለው ዋጋ እጅግ ከፍተኛ ነበር። “ዘ አፍሪካ ሪፖርት” እንደገለጸው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሞተዋል፣ የትግራይ ኢኮኖሚ ወድሟል፣ የትህነግ የፖለቲካ ሥልጣንም ክፉኛ ተዳክሟል። ብዙ የትግራይ ሰዎች ክልሉን ወደ አውዳሚ ግጭት መርቷል በሚል ፓርቲውን በግልጽ ወቅሰዋል። ከዛም አልፎ አንዳንድ ተንታኞች ስለሚመጣው “ከትህነግ በኋላ ያለ ዘመን” ማውራት ጀምረዋል።

ከፕሪቶሪያ ስምምነት በኋላ በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ተቋቋመ። አስተዳደሩም አንጋፋው የትህነግ ሰው በሆኑት ጌታቸው ረዳ ይመራ ነበር። ጌታቸው ግባቸው በአስተዳደራዊ ማሻሻያዎች አማካኝነት በክልሉ የዲሞክራሲ ምህዳርን መክፈት እንደሆነ በግልጽ ተናግረው ነበር። ይሁን እንጂ እነዚህ ማሻሻያዎች ትህነግ በትግራይ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሕይወት ላይ የነበረውን የቆየ የበላይነት እንደቀነሱት ተንታኞች ጠቅሶ አቶ ጌታቸውና አመራራቸው እንዴት እንድተሸረሸሩ ጽሁፉ ያስረዳል።

በዚሁ ስሜት ብዙም ሳይቆይ ትህነግ ቁጥጥሩን መልሶ ለማግኘት ተንቀሳቀሰ። እንደ “ዘ አፍሪካ ሪፖርት” ዘገባ ከሆነ ፓርቲው በመጋቢት ወር የትግራይ መከላከያ ኃይልን በመጠቀም ጌታቸውን ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንትነት አነሳ። የትህነግ መሪዎች ጌታቸውን የከዳተኛ እና የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ደጋፊ በማለት ከሰሱ። ይህ እርምጃ ከፌዴራል መንግሥት ጋር ያለውን ውጥረት በእጅጉ ያባባሰው ሲሆን ዳግም ጦርነት ሊቀሰቀስ ይችላል የሚለውን ሥጋትም አድሶታል።

በተመሳሳይ ሰዐት ትህነግ ከትግራይ ውጭ ድጋፍ መፈለግ ጀመረ። ፓርቲው የኤርትራንና የአማራውን አማፂ ንቅናቄ ፋኖን ጨምሮ ከሌሎች የፌዴራል መንግሥት ጠላቶች ጋር ግንኙነት እንደመሰረተ ተነግሯል። ኤርትራ እና ፋኖ በቅርቡ በነበረው ጦርነት ትህነግን ተዋግተው ስለነበር ይህ አዲ ግንኙነት ብዙ ታዛቢዎችን አስገርሟል። በኅዳር ወር የፌዴራል መንግሥት ትህነግና ኤርትራ በምስራቅ አማራ ወሎ ውስጥ ለተከፈተው መጠነ ሰፊ የፋኖ ጥቃት ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ከስሷል። ምንም እንኳን ሦስቱም ወገኖች መደበኛ ትብብር ማድረጋቸውን ቢክዱም፤ ዘ አፍሪካ ሪፖርት ብዙ ምንጮች ክሱን ተአማኒ እንደሚያደርጉት ገልጿል።

ከታጣቂዎቹ ራሳቸው የሚወጡ መግለጫዎች ቢያንስ መደበኛ ያልሆነ ቅንጅት ሊኖር እንደሚችል ይጠቁማሉ። የአንድ የወሎ ፋኖ አዛዥ ለዘ አፍሪካ ሪፖርት እንደተናገሩት “ምንም እንኳን ይፋዊ ጥምረት ባይኖርም በአማራ፣ በትግራይ እና በኤርትራውያን መካከል አንድነት መፈጠሩ ‘ኃጢአት አይሆንም’ ” ብለዋል። በተመሳሳይ ሁኔታ አንድ የትህነግ ሰራዊት አዛዥ በወሎው ጥቃት ውስጥ መሳተፋቸውን በግልጽ ቢክዱም ዋናው ጠላት ፋኖ ወይም ኤርትራ ሳይሆኑ የፌዴራል መንግሥት መሆኑን አክለው ገልጸዋል። በእንደዚህ ዓይነት መግለጫዎች ምክንያት አንዳንድ ተንታኞች አሁን ‘ሊፈጠር ስለሚችል’ “የሰሜን ጥምረት” ማውራት ጀምረዋል። ሆኖም ግን የትግራይ ተወላጁ ደራሲና የፖለቲካ ተንታኝ ዳንኤል በርሄ የዚህ ትብብር ጥንካሬና ዘላቂነት አሁንም አስተማማኝ እንዳልሆነ ይገልጻል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በትግራይ ውስጥ ያለው ችግር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል። በጥቅምት ወር በተራ የትህነግ ወታደሮች መካከል መጠነ ሰፊ ተቃውሞ ተቀሰቀሰ። ወታደሮቹ ዝቅተኛ ደመወዝ፣ የከፋ የኑሮ ሁኔታ እና የቀድሞ ጦርነት ዘማቾች ችላ መባልን በመቃወም ቅሬታቸውን አሰምተዋል። መንገዶችን ዘግተዋል፣ ከፍተኛ አዛዦችንም በግልጽ ተጋፍጠዋል። ምንም እንኳን ባለሥልጣናቱ በመጨረሻ ሥርዓት ቢያስከብሩም፣ ተቃውሞው በሰራዊቱ ውስጥ ያለውን ብስጭት አሳይቷል።

ለዚህ ምላሽ ለመስጠት የፌዴራል መንግሥት በክልሉ ላይ ያለውን ጫና አጠናክሯል። ዳንኤል በርሄ እንዳብራሩት ከአዲስ አበባ ይላክ የነበረው የፌዴራል ፈንድ ቀንሷል፣ የነዳጅ አቅርቦትን ገደብ ተደርጎበታል፣ እንዲሁም ከትህነግ ጋር ግንኙነት ያለውንና ግዙፍ የንግድ ተቋም የሆነውን የኤፈርት (EFFORT) ኩባንያዎችን የባንክ ሒሳብ አግዷል። እነዚህ እርምጃዎች የትግራይን የኢኮኖሚ ቀውስ የበለጠ አባብሰዋል። ይህ ጽሁፍ በዘ አፍሪካ ሪፖርት ከታተመ በሁዋላ በኘዘብ ተቋማቱ ላይ የተጣለው ዕገድ ተነስቷል።

በተመሳሳይ ጊዜ በትህነግ አመራር ውስጥ ያለው ክፍፍል እየሰፋ ሄዷል። በምክትል ሊቀመንበሯ ፈትለወርቅ ገብረእግዚአብሔር የሚመራው አንዱ ወገን ከፌዴራል መንግሥት ጋር የሚደረግ ፍጥጫ የማይቀር መሆኑን ያምናል። በአለም ገብረዋህድ የሚመራውና ጌታቸውን በጊዜያዊ ፕሬዝዳንትነት የተኩት ታደሰ ወረደ የሚደግፉት ሌላኛው ወገን ደግሞ ጥንቃቄ የተሞላበት አካሄድን ምናልባትም ከአዲስ አበባ ጋር አዲስ ውይይት መጀመርን ይመርጣሉ።

እነዚህ አለመግባባቶች በትህነግ ሰራዊት ውስጥም ተንጸባርቀዋል። በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ወታደሮች የሬዲዮ ጣቢያዎችን ተቆጣጥረው በመቀሌ የሚገኘውን የፕሬዝዳንት ታደሰን ቢሮ ከበው ነበር። ባለሥልጣናት ክስተቱ ከደመወዝ ቅሬታ ጋር የተያያዘ ነው ቢሉም ሌሎች ታዛቢዎች ግን ለ”ዘ አፍሪካ ሪፖርት” እንደተናገሩት ይህ የጥንካሬ ማሳያ በፅንፈኛ አዛዦች የተደረገ ነው። አንድ ምንጭ ደግሞ ጄኔራሎቹ በተጨባጭ ቁጥጥሩን ይዘዋል በትግራይ ውስጥ ሲቪል አገዛዝ ላይኖር ይችላል እስከማለት ደርሰዋል።

ትህነግ አሁን ባለበት ደካማ አቋምም ቢሆን የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ፈራሚ እንደመሆኑ መጠን ሕጋዊና ተምሳሌታዊ ጠቀሜታ አለው። የምርጫ ቦርድ በግንቦት ወር የፓርቲውን ሕጋዊ ሰውነት ለመሰረዝ የወሰነው ውሳኔ በተለይ አደገኛ ተደርጎ የሚታየም ከዚሁ አንጻር ነው። አገራዊ ምርጫ በሰኔ ወር እንዲካሄድ በታቀደበት ሁኔታ ትህነግን ማግለል ሌላ ቀውስ ሊያስነሳ እንደሚችል ተንታኞች ያስጠነቅቃሉ። አንድ በኢትዮጵያ የሚገኝ ተንታኝ ለ”ዘ አፍሪካ ሪፖርት” እንደተናገረው የፓርቲው ሕጋዊ ሰውነት ካልተመለሰ በስተቀር ዳግም ጦርነት የማይቀር ሊሆን ይችላል። ምንም እንኳን ሁለቱም ወገኖች ጦርነትን በግልጽ ባይፈልጉም ለመደራደር ፈቃደኛ አለመሆናቸው ኢትዮጵያ በድጋሚ ወደ አለመረጋጋት እያመራች መሆኗን ይጠቁማል።

ፌስቡክ፡ https://web.facebook.com/addisreporternews/
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter11
X፡ https://x.com/addisreporter
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393

Share and Enjoy !

Shares

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

Share post:

Subscribe

spot_imgspot_img

Popular

More like this
Related

የአዲስ አበባ ሕዝብ የእናት ሀገር ጥሪ ተሳትፎና ኮሎኔል መንግሥቱ

የእናት አገር ጥሪ ከተደረገ በኋላ መላው የአዲስ አበባ ሕዝብ...

ቢሾፍቱ አለምአቀፍ አየር ማረፊያ፤ ኢትዮጵያን ወደ መፃኤ ዘመን የሚያሻግር የሎጂስቲክስ አብዮት

ኢትዮጵያ ከቢሾፍቱ ሰማይ ስር የኢኮኖሚና የሎጂስቲክስ ካርታዋን እንደገና ለመሳል...

“ጥርስ የሌለው ውሻ” የሆነው የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና የዓለም መፃኢ እጣፈንታ

አዲስ ሪፖርተር - ፕሬዛዳንት ትራምፕ አሜሪካን ከተባበሩት መንግስታት ደርጅት...

በዘመነ ትራምፕ ጫና ውስጥ የወደቀችው ሶማሊያ እና ለሶማሌ ላንድ ተስፋን ያለመለመው አዋጅ

አዲስ ሪፓርተር - ከሶማሌላንድ የሉዓላዊነት ጥያቄ እና ከእስራኤል እውቅና...