ደሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ ምርጫ ቦርድ የሁመራ፣ የጸገዴ፣ የወልቃይት፣ የጠለምትና የራያ አላማጣ ምርጫ ከልሎች ከትግራይ ውጭ እንዲሆኑ የወሰነውን ውሳኔ በመቃወም ምርጫ ሊሳትፈ እንደማይችል አስጠነቀቀ። ውሳኔውን ሕገ መንግስቱን የጣሰ እንደሆነ አመልክቷል። የደብዳቤውን ሙሉ ቃል ያንብቡ።
ጉዳዩ፡- የፌዴሬሽን ምክር ቤት በምርጫ ክልሎች ላይ ያስተላለፈው ውሳኔ ዳግም እንዲታይ መጠየቅ ይመለከታል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥር 25 ቀን 2018 ዓ.ም. ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ደረሰኝ ባለው ደብዳቤ መሰረት፤ በማድረግ በአማራና በትግራይ ክልሎች መካከል “አወዛጋቢ” በተባሉ አካባቢዎች በሚገኙ የምርጫ ክልሎች ላይ ያስተላለፈው ውሳኔ፤ የሀገሪቱን ሕገ-መንግስታዊ ስርዓት መሰረት የሚንድ፣ ተቋማዊ ነፃነትን የሚደፈጥጥና በደረጃው “ሕገ-መንግስታዊ ስርዓት አልበኝነትን” የሚያውጅ ነው።
በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ-መንግስት አንቀጽ 62 ስር ለፌዴሬሽን ምክር ቤት የተሰጡት ስልጣንና ተግባራት የሕገ-መንግስት ትርጓሜና የክልሎች ወሰን ክርክርን ከመፍታት አይዘልሉም። ምክር ቤቱ የምርጫ ክልሎችን የማዋቀርም ሆነ ከነበሩበት አስተዳደራዊ መዋቅራቸው ውጭ በፌዴራል መንግስት ስር እንዲሆኑ የመወሰን ምንም ዓይነት ሕገ-መንግስታዊ ውክልና የለውም። ይህ ውሳኔ ምክር ቤቱ ራሱን ከሕግ በላይ አድርጎ መሾሙንና የፌዴራል ስርዓቱ በጠራራ ፀሐይ እየተገረሰሰ መሆኑን ያሳያል።
ማንኛውም የክልል ወሰን ክርክር መፍትሔ ሊያገኝ የሚገባው በሕገ-መንግስቱ አንቀጽ 48 በተደነገገው መሰረት ብቻ ነው። ይህ ሕጋዊ ሂደት ሳይጠናቀቅ በሕዝብ-ውሳኔ ይቁም ሳይደረግ፤ “ምርጫው በፌዴራል መንግስት ይፈጸም” የሚለው ትእዛዝ፤ የክልል አስተዳደርን በጉልበት የመንጠቅ (Administrative Annexation) ሙከራ ነው።
ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአንቀጽ 102 መሰረት ተጠሪነቱ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሆነና ከማንኛውም ተፅዕኖ ነፃ መሆን ያለበት ተቋም ነው። የፌዴሬሽን ምክር ቤት በፖለቲካዊ ፍላጎት ተገፋፍቶ በቦርዱ የሥራ መመሪያና አደረጃጀት ላይ ጣልቃ መግባቱ፤ ተቋሙን የፖለቲካ መጠቀሚያ ከማድረጉም በላይ የምርጫውን ተዓማኒነት ከወዲሁ አጠራጣሪ አድርጎታል
ይህ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ ተከትሎም ሆነ እሱን ተከትሎ የመጣው የምርጫ ቦርድ ድርጊት ግልጽ የስልጣን አላግባብ መጠቀም (Abuse of Power) ማረጋገጫና በሕግ ፊት ‘ውድቅና የማይጸና’ (Null and Void) ነው።
ደሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ ይህንን ሕገ-ወጥ ድርጊት በጽኑ ይኮንናል! የፌዴሬሽን ምክር ቤት የጀመረውን ሕገ-አልባ ዳንኪራ በአስቸኳይ እንዲያቆም እና ለሕገ-መንግሥቱ የበላይነት እንዲገዛ ያሳስባል። በዚህ ሕገ-አልባ የፖለቲካ ትዕይንት የሚፈታ አንድም ችግር እንደሌለ ድርጅታችን ስምረት ስለሚገነዘብ፤ ማስተካከያ እርምጃ እስካልተወሰደ ድረስ በምርጫውም ሆነ በመሰል ሕገ-ወጥ ድርጊቶች ላይ የማይሳተፍ መሆኑን መላው የትግራይ ሕዝብ እንዲያውቀው እንፈልጋለን። የሕዝብን ሉዓላዊነት እና ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓቱን ለማስጠበቅ ድርጅታችን አስፈላጊውን ሕጋዊና ፖለቲካዊ ትግል ለማድረግ የማይነጥፍ ቁርጠኝነት ያለው መሆኑን በድጋሚ እናረጋግጣለን።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addisreporternews
ስልክ ቁጥር፡ +251116393393






