አዲስ ሪፖርተር – የቀድሞ የፌደሬሽን ምክር ቤት አፋ ጉባኤ እና የትህነግ ስራ አስፈፃሚ አባል የነበሩት ወይዘሮ ኬሪያ ኢብራሂም ‹‹በትግራይ የአስቸኳይ ጊዜ መታወጅ አለበት›› በሚል ጥሪ ማስተላለፋቸው ተሰማ። የትግራይ ተወላጆች በሙሉ አንድ ሆነው ለትግራይ ሕዝብ እንዲደርሱለት አሳሰቡ፡፡
የቀድሞዋ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ ወይዘሮ ኬሪያ ኢብራሂም ዛሬ ባደረጉት ቃለ ምልልስ ‹‹ለህዝብ ሲባል የጦርነት በሮች ሁሉ መዘጋት አለባቸው፡፡ ለዚህ ደግሞ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ የክልሉ ተወላጆች ጥረት ማድረግ ይገባቸዋል፡›› ብለዋል፡፡ ኬሪያ ወጋህታ ከተሰኘው ጋር ባደረጉት በዚህ ቃለ ምልልስ ‹‹የትግራይ ተወላጆች አሰላለፋችንን ማስተካከል አለብን፡፡
ከፌዴራል መንግስት ጎን በመቆም ህዝባችንን ከችግር ማላቀቅ ይኖርብናል›› ያሉ ሲሆን በትግራይ ክልል ውስጥ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጅ እንዳለበትም አስረድተዋል፡፡ ንግግራቸውን ሲቀጥሉም ‹‹የፌዴራል መንግስት ሊመልሳቸው የሚችላቸውን ጥያቄዎች መመለስ መቻል አለበት ብዬ አስባለሁ፡፡ ይህንን እንዲመልስ መቃወም ሳይሆን ከጎኑ መቆም አለብን›› በማለትም ገልፀዋል፡፡
የትግራይ ህዝብ ከአገሩ ጋር የመዋጋት ታሪክ እንደሌለው የጠቀሱት ወይዘሮ ኬሪያ የህወሀት ቡድን ግን ጦርነት ለማስነሳት እየሞከረ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡ ጨምረውም ‹‹የትግራይ ህዝብ ከአገሩ ጋር የሚጋጭበት ምንም አይነት ሁኔታ የለም፡፡ እንዲህ አይነት ታሪክም የለውም፡፡ ህዝቡ አገሩን የሚወድ በመሆኑ ከፌዴራል መንግስት ጋር መቆም ይኖርበታል፡›› በማለትም ገልፀዋል፡፡
የቀድሞዋ አፈጉባኤ ሲቀጥሉም ‹‹የትግራይ ህዝብና ምርድ የጦር ሜዳ እንዳይሆን መጠንቀቅ አለብን፡፡ የጥፋት ሀይሎችን መዋጋትም አለብን፡፡ ትግራይ የጦር ሜዳ መሆን የለባትም፡፡ ስለዚህ ይህ እንዳይከሰት አሰላለፋችንን ማስተካከል ያስፈልጋል›› ብለዋል፡፡ በማስከተልም ‹‹እኔ ሰላም ይምጣ፣ ጦርነት አቁሙ እያልኩ ነው፡፡
ሰላም በትግራይ እንዲሰፍን ችግሩን በህጋዊ መንገድ መፍታት ካልተቻለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጅ አለበት፡፡ ምክንያቱም ትግራይ ውስጥ ስርአት አልበኝነት አለ፡፡ ህዝቡ ለጦርነት ገንዘቡን እንዲለግስና በጦርነቱ ውስጥ እንዲሳተፍ ለማስገደድ እየተሞከረ ነው›› በማለትም አስረድተዋል፡፡
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addisreporternews
ስልክ ቁጥር፡ +251116393393






