አዲስ ሪፖረተር – በኢትዮጵያ ለማኅበረሰቡ የሚቀርብ ብዙ መጠን ያለው የወተት ምርት ጥቅም ላይ የሚውል ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ ለሽያጭ የሚቀርብ አምስት በመቶ ብቻ የሚሆነው የወተት አቅርቦት ጥራቱ የጠበቀ መሆኑን የኢትዮጵያ ምግብና መድሐኒት ባለሥልጣን ለአዲስ ሪፖርተር አስታውቋል፡፡
በባለስልጣን መስሪያ ቤት የእንሰሳት ተዋፅዖና አልሚ ምግቦች ኢንስፔክሽን ዴስክ ኃላፊ አቶ መሐመድ ሁሴን ለአዲስ ሪፖርተር እንደተናገሩት፤ በሀገሪቱ አጠቃላይ የወተት ምርት አቅርቦት ላይ የጥራት ችግር መኖሩን ተናግረዋል።
ማንኛውም ሰው እንደፈለገ ወተት እያዞረ መሸጥ እንደማይችል፣ ይህን የመረዳትና የማክበር የግንዛቤ ጉድለት በማሕበረሰቡ ዘንድ መኖሩን የገለጹት ኃላፊው፤ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የወተት ምርትና ሽያጭ ከሚያስፈልገው ከፍተኛ ጥንቃቄ አንፃር በጀሪካንና በሌሎችም ባልተፈቀዱ ዕቃዎች ማጓጓዝ ጥራቱን ከማጓደል ባሻገር ለበሽታ አምጪ ተዋህስያን የሚያጋልጥ መሆኑን አስረድተዋል። አክለውም፤ “ዘርፉ ያላደገ በመሆኑ የሚስተዋሉ የጥራት ችግሮችን ሙሉ ለሙሉ ለመቅረፍ አልተቻለም” ብለዋል።
ከዚህ ጋር ተያይዞ በወተት ምርቶች በተለይም በባህላዊ መንገድ ለሕብረተሰቡ የሚቀርቡ ምርቶች ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚሹ በመሆናቸው፤ ወተት አቅራቢዎች በቂ ስልጠናዎችን በመውሰድ ዘመናዊ አሰራሮችን ሊከተሉ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ለዚህም በዋናነት ከሚስተዋሉ ችግሮች አንጻር የመኖ በበቂ ሁኔታ አለመቅረብ እና የእንሰሳት አያያዝ ተጠቃሽ መሆኑን አስረድተዋል። ይህ ማለት ሙሉ ለሙሉ ጥራት የጎደላቸዉ የወተት ምርቶች ገበያ ላይ አሉ ማለት እንዳልሆነ እና ጥራት ያላቸው የወተት ምርቶች ስለመኖራቸው አንስተዋል።
በባለሥልጣኑ በኩል የተጀመሩ የቁጥጥር ሥራዎችን በአዲስ አበባ እና በሌሎች ክልሎችም ተጠናክረው እንደሚሰሩም ኃላፊው ጨምረው ገልጸዋል። የዴስክ ኃላፊው አክለውም ባለሥልጣኑ የወተት ጥራትን ለማስጠበቅ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ ሕጋዊ ሂደቱን በተመለከተ ለማሕበረሰቡ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባ ገልጸዋል።






