አዲስ ሪፓርተር – የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በአየር ኃይል አንድ (Air Force One) ውስጥ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ በኮሎምቢያው ፕሬዝዳንት ጉስታቮ ፔትሮ ላይ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ ሰንዝረዋል። ትራምፕ የቬንዙዌላው መሪ ኒኮላስ ማዱሮ በአሜሪካ ልዩ ኃይል ተይዘው ወደ ኒውዮርክ መወሰዳቸውን ተከትሎ በሰጡት በዚህ መግለጫ፣ ቀጣዩ ኢላማ ኮሎምቢያ ልትሆን እንደምትችል አመልክተዋል። ፕሬዝዳንቱ ጉስታቮ ፔትሮን “በሽታኛ” እና “ኮኬይን በማምረት ለአሜሪካ የሚሸጥ ሰው” ሲሉ የገለጹ ሲሆን፣ ይህ ድርጊታቸውም ብዙ እንደማይቀጥል ዝተዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኮሎምቢያ ውስጥ “የኮኬይን ፋብሪካዎች” እንዳሉ በመጥቀስ፣ አሜሪካ በሀገሪቱ ላይ ወታደራዊ ዘመቻ ልታካሂድ ትችላለች ወይ ተብለው ሲጠየቁ “ሀሳቡ ጥሩ ይመስለኛል” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል። ይህ ንግግር በላቲን አሜሪካ ሀገራት ዘንድ ከፍተኛ ስጋትን የፈጠረ ሲሆን፣ የኮሎምቢያው ፕሬዝዳንት ጉስታቮ ፔትሮ በበኩላቸው ትራምፕ በሀገራቸው ሉዓላዊነት ላይ ጣልቃ እየገቡ መሆኑን በመጥቀስ “መሰረተ ቢስ ስም ማጥፋት ይቁም” ሲሉ በጠንካራ ቃላት አጣጥለውታል።
በተመሳሳይ መግለጫ ላይ ትራምፕ የአርክቲክ ግዛቷን ግሪንላንድን ከአሜሪካ ብሄራዊ ደህንነት አንጻር ለመቆጣጠር ያላቸውን ፍላጎት በድጋሚ አንስተዋል። ዴንማርክ የግዛቷን ደህንነት የመጠበቅ አቅም እንደሌላት የገለጹት ትራምፕ፣ ግሪንላንድ ለአሜሪካ ስልታዊ ጠቀሜታ እንዳላት አስምረውበታል። ይሁን እንጂ ይህ ንግግር ከዴንማርክ እና ከግሪንላንድ መሪዎች ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሞታል። የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሜቴ ፍሬድሪክሰን “ግሪንላንድ ለሽያጭ የቀረበች አይደለችም” ሲሉ አሜሪካ በወዳጅ ሀገራት ላይ የምታደርገውን ዛቻ እንድታቆም አሳስበዋል።
የግሪንላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ጄንስ-ፍሬድሪክ ኒልሰንም የትራምፕን ንግግር “ለዲሞክራሲያዊ ህዝብ ክብር የማይሰጥ” ሲሉ ወቅሰዋል። ኖርዌይ፣ ፊንላንድ እና ሌሎች የሰሜን አውሮፓ ሀገራትም የዴንማርክን ሉዓላዊነት እንደሚደግፉ በማሳወቅ፣ በአርክቲክ ቀጠና ያለው ሰላም በትራምፕ ንግግሮች እንዳይታወክ ስጋታቸውን ገልጸዋል። ይህ የትራምፕ አዲስ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አዝማሚያ “የሞንሮ ዶክትሪን” በሚል መጠሪያ እየተጠቀሰ ሲሆን፣ አሜሪካ በጎረቤት ሀገራት ሀብትና ፀጥታ ላይ ያላትን ቁጥጥር ለማስፋፋት የምታደርገው ጥረት እንደሆነ እየተነገረ ይገኛል።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/addisreporter
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393






