አዲስ ሪፖርተር – “መንግሥትም የህዝቡን የማንነት እና የራስ አስተዳደር ጥያቄ ዓለማቀፋዊ ተቀባይነት ባለው አሰራር በሕገ መንግስቱ መሰረት እንዲፈታ እና ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑ ያልተዋጠለት ወያኔ ለአራተኛ ጊዜ በሕዝባችን ላይ የእብሪት ወረራ በመፈፀም ሂደቱን ቢያደናቅፈውም ውሳኔው የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ኢትዮጵያ ውስጥ የጉልበት አማራጭ እንደማያዋጣ እና በየትኛውም መመዘኛ ተቀባይነት እንደማይኖረው ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ እና የፌደሬሽን ምክር ቤትም ሆነ የቦርዱ ውሳኔ ተገቢነት ያለው መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው” ሲል የወሎ ራያ አማራ ማንነት እና ወሰን አስመላሽ ኮሚቴ አስታወቀ።
ኮሚቴው ለአዲስ ሪፖርተር የላከው መግለጫ እንደሚከተለው ይነበባል።

የፌደሬሽን ምክር ቤት በቁጥር ፌዴም/አፈ/5/13138 በቀን 25/05/2018 ዓ/ም ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በፃፈው ደብዳቤ ክርክር የተነሳባቸው የሁመራ፣ የአዲረመጥ፣ የኮረም ወፍላ፣ የጠለምት እና የራያ አላማጣ ምርጫ ክልሎች ከትግራይ ክልል ውጪ ሆነው ለብቻቸው በቀጥታ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ እንዲደረግ ያስተላለፈውን ውሳኔ ተከትሎ የካቲት 16/2018 ዓ/ም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያስተላለፈው ውሳኔ የሕዝባችንን የዘመናት ጥያቄ ለመፍታት መንግስት የጀመረውን ጥረት አንድ እርምጃ ወደ ፊት የሚያራምድ በጎ ውሳኔ እንደሆነ በጽኑ እናምናለን።
ውሳኔው በኢፌዴሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 38 ንዑስ አንቀጽ 1 ፊደል ተራ (ሀ)፣ (ለ) እና (ሐ) በሰፈረው የሕግ ድንጋጌ ለማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የተሰጠውን ሕገ መንግስታዊ መብት የሚያጎናጽፍ ከመሆኑም ባሻገር በ2013 ዓ/ም በተካሄደው 6ኛ ጠቅላላ ሃገራዊ ምርጫ የአካባቢው ነዋሪዎች ባለመሳተፋቸው እና ወኪሎቻቸውን መምረጥ ባለመቻላቸው ምክንያት አጥተውት የነበረውን ዲሞክራሲያዊ መብት መልሶ የሚያጎናጽፍ እና ያለፈውን ስብራት የሚጠግን ታሪካዊ ውሳኔ እንደሆነም በእጅጉ እናምናለን፡፡
ይህ ውሳኔ በኢፌዴሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 46 ንዑስ አንቀጽ 2 እና በፌዴሬሽን ምክር ቤት የክልሎችን አወቃቀር አስመልክቶ በወጣው አዋጅ ቁጥር 7/1984 የኢትዮጵያ ክልሎች አወቃቀር በአሰፋፈር ሁኔታ፣ በቋንቋ፣ በማንነት እና በሕዝቦች ፈቃድ ላይ የተመሰረተ ይሆናል በሚል የሰፈረውን የሕግ ድንጋጌ በሚፃረር መልኩ በኃይል ወደ ትግራይ ክልል እንዲካለሉ ለተደረጉት የትግራይ ክልል አጎራባቾቹ የራያ፣ የዛታ፣ የወፍላ እና የኮረም ሕዝቦች ላለፉት ሰላሳ ዓመታት ይደርሱባቸው ከነበሩት እና አሁንም ተጠናክረው እየቀጠሉ ካሉት መዋቅራዊ እና ስልታዊ ጥቃቶች ለመላቀቅ የሚያስላቸውን ምቹ መደላድል የሚፈጥር እና የቦርዱን ተቋማዊ ጥንካሬ እና ገለልተኝነት ፍንትው አድርጎ ያሳየ ውሳኔ ነው፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ እብሪተኛው ወያኔ ጥቅምት 24/2013 ዓ/ም በሀገር መከላከያ ሰራዊት ላይ በፈፀመው ታሪክ ይቅር የማይለው ክህደት ምክንያት በተካሄደው ጦርነት እና በተገኘው አኩሪ ድል ሕዝባችን በመስዋዕትነት የደመቀ በደም የታተመ ሰላም እና አንፃራዊ ነፃነት ማገኘቱ፣ መንግሥትም የህዝቡን የማንነት እና የራስ አስተዳደር ጥያቄ ዓለማቀፋዊ ተቀባይነት ባለው አሰራር በሕገ መንግስቱ መሰረት እንዲፈታ እና ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑ ያልተዋጠለት ወያኔ ለአራተኛ ጊዜ በሕዝባችን ላይ የእብሪት ወረራ በመፈፀም ሂደቱን ቢያደናቅፈውም ውሳኔው የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ኢትዮጵያ ውስጥ የጉልበት አማራጭ እንደማያዋጣ እና በየትኛውም መመዘኛ ተቀባይነት እንደማይኖረው ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ እና የፌደሬሽን ምክር ቤትም ሆነ የቦርዱ ውሳኔ ተገቢነት ያለው መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡
በመጨረሻም የፌደሬሽን ምክር ቤት ውሳኔን ማዕከል በማድረግ ቦርዱ ይፋ ያደረገው ውሳኔ የጉልበት አማራጭን ጨርሶ የሚዘጋ እና የዜጎችን ሕገ መንግሥታዊ መብት የሚያስከብር በጎ እርምጃ በመሆኑ የራያ፣ የወፍላ እና የኮረም ሕዝቦች ማንነታችን አማራ ነው በማለታቸው ምክንያት ለዘመናት ይደርስባቸው የነበረው እና አሁንም ድረስ መቋጫ ያላገኘው መዋቅራዊ እና ስልታዊ ደባ የሚገታበትን ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር በእነዚህ አካባቢዎች የሚደረገው ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብቻ ሳይሆን ለአማራ ክልል ምክር ቤት ጭምር እንዲሆን ከወዲሁ እንጠይቃለን።
የወሎ ራያ አማራ ማንነት እና ወሰን አስመላሽ ኮሚቴ
የካቲት 17/2018 ዓ/ም ቆቦ
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addisreporternews
ስልክ ቁጥር፡ +251116393393






