አዲስ ሪፖርተር (ጎንደር)- የጎንደር አማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ቅርንጫፍ ጋዜጠኛ ደስታ ካሳ በፋኖ ታጣቂዎች ታፍኖ ከወር በሁዋላ ሶስት መቶ ሺህ ብር ከፍሎ መፈታቱን መዋጮ ሲያሰባስቡ የነበሩ ወገኖችን ጠቅሶ የአዲስ ሪፖርተር የጎንደር ተባባሪ አመለከተ። አጋቾቹ የጋዜጠኛው መታገት ለመከላከያ፣ ለሚዲያና ለአካባቢ የጸጥታ ኃይሎች ቢነገር በአንድ ጥይት እንደሚገድሉት በመዛት ጉዳዩ ሳይዘገብ ቆይቷል።
ደስታ የታገተው ከጎንደር ወደ ባህር ዳር ሲሄድ ማክሰኚት ላይ ነው። ማክሰኚት ከጎንደር 18 ኪሎሜትር ላይ ትገኛለች።በተደጋጋሚ ሰሊጥ የጫኑ ከባድ የጭነት ተሽከርካሪዎች ከሚቃጠሉበት ከዚህ ቦታ ላይ የታገተው ደስታ ሶስት መቶ ሺህ ብር እንዲከፍል፣ ካልከፈለ እንደሚገድሉት በተነገርው መሰረት ቤተሰቦችቹና ወዳጆቹ እንዲሁም ባልደረቦቹ የከተማዋ ነዋሪዎችን በማስተባበር የተጠየቀውን ገንዘብ ከፍለው አንድ ወር ግድም ከተቀመጠበት ጫካ ወጥቷል።
አጋቾቹ የፋኖ ኃይሎች፣ በስልክ በተደረገ ግንኙነት አማካይነት ብሩን በሰው ወዳሉበት ግድም ተወስዶ ከተረከቡ በሁዋላ የተፈታው ደስታ ነጻ ከሆነ በሁዋላም ቢሆን ምንም ዓይነት መረጃ እንዳይሰጥ በመከልከሉ በስጋት ምንም ማለት እንደማይፈልግ ቅረብ የሆኑት ለጎንደር ተባባሪያችን ነግረውታል።
“ክላሽ ወድረው ካሉት ስፍራ የተላከላቸውን ገንዘብ ይዞ ከሄደ ሰው ሲቀበሉ፣ ያስቀመጠው ሰው ፊቱን አዙሮ እንዲሄድ አዘዙት። ዞሮ እንዳይመለከት አስጠነቀቁት።” በማለት ብሩን ካደረሰው ሰው የሰሙትን ያስረዱ እንዳሉት ወዲያው ደስታ ነጻ ሊሆን ችሏል። አጋቾቹ ገንዘብ ከመጠየቃቸው ሌላ እገታ የሚፈጽሙበት ፖለቲካዊ ምክንያት እንደሌላችውም ለማወቅ ተችሏል።
ደስታ በአሁኑ ሰዓት መደበኛ ስራውን እያከናወነ ሲሆን። ከምስክሮቹ እንደተሰማው ሞባይል የያዘ፣ ንጹህ ልብስ የለበሰ፣ እንዲሁም ጥቆማ የተላለፈበት ሰው እንደሚታገት ገልጸዋል።
ፌስቡክ፡ https://web.facebook.com/addisreporternews/
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter11
X፡ https://x.com/addisreporter
ስልክ ቁጥር፡ +251981866434 / +251116393393






