አዲስ ሪፖርተር – የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) የዓለምአቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) የአባል ሀገራትን ኮታ በ50 በመቶ ለማሳደግ ያሳለፈውን ውሳኔ በፍጥነት ተፈፃሚ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።
ማዕከላዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ ለድርጅቱ ጥያቄ ያቀረቡት በአሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ በተካሄደው የዓለም ባንክ እና የዓለም የገንዘብ ድርጅት (IMF) ዓመታዊ ስብሰባ ጎን ለጎን በተካሄደው የአፍሪካ አገራት ቡድን ስብሰባ በተሳተፉበት መድረክ ሲኾን ድርጅቱ የአባል አገራት ኮታ ለመጨመር የወሰደው እርምጃ በኢትዮጵያ በኩል ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት እንዳለው ገልፀዋል።
ኢትዮጵያ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ያለውን የፋይናንስ ደህንነት ፣ ፍትሐዊነት እንዲሁም የሐብት ክፍፍል እንዲኖር ፍላጎት እንዳለ ጠቅሰው አሁን ላይ ታዳጊ አገራት በገንዘብ ተቋሙ የሚኖራቸውን ውክልና እንዲያድግ ይሁንታ በመፈጠሩ የድርጅቱን ውሳኔ አድንቀዋል።
በተለይም ለአባል አገራቱ የሐብት ተደራሽነት ለማስፋት እንዲሁም በድርጅቱ ፍትሐዊ ውክልና እንዲኖራቸው በማስቻል ረገድ ከፍተኛ የኢ-ፍትሃዊነት ጥያቄ ሲነሳበት እንደነበር በመግለፅ የውክልና ሂደቱን ወደ ተግባር እንዲገባ እንዲሁም የኮታና የውክልና አለመመጣጠን ላይ ያሉ ክፍተቶች በአፋጣኝ እንዲስተካከል ለገንዘብ ተቋሙ ኃላፊዎች ጥያቄ አቅርበዋል።
እዮብ ተካልኝ አክለውም በአፍሪካ ያሉ አገራትን ጨምሮ በሌሎች ክፍለ ዓለማት ያሉ ታዳጊ አገራት ድርጅቱ የሰጣቸው የኮታ ድልድል ጉዳይ እስካሁን ትኩረት አለማግኘቱ አሉታዊ ተፅእኖ ሲፈጥር መቆየቱን ገልፀው የተሰሚነት ደረጃቸውንና ድምፅ የመስጠት ውስንነት በስፋት ሲያጋጥም እንደነበር አምልክተዋል።
የብሄራዊ ባንክ ገዢ የውሳኔ አሰጣጥ መዋቅር ውስጥ ዝቅተኛ ውክልና ላላቸው አገሮች ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ መኾኑን አፅንኦት ሰጥተዋል። በተለይም ፍትሃዊ፣ ሚዛናዊ እና ሁሉን አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት እንዲፈጠር ድርጅቱ የበኩሉን እንዲወጣ አሳሰበዋል።




