የወልቃይት-ጠገዴ-ሰቲት ሁመራ፣ እና የጠለምት ሕዝብ በህዝብና በሀገር መስዋዕትነት የተገኘውን ድል ለማጽናት በራሱ አቅም ሰላምና ጸጥታውን አስፍኖ የሚገኝ አካባቢ በመሆኑ፣ ምርጫ ላለማካሄድ ምንም አይነት ተጨባጭ ምክንያት ሳይኖር አንድ ሙሉ የምርጫ ዘመን ያለ በጀትና የፖለቲካ ውክልና እንዲያሳልፍ መደረጉ ታሪካዊ በደል መሆኑ እየታወቀ አሁንም በድጋሚ በተለያዩ ሰበቦች ሕዝቡን ከምርጫ በማግለል ቀጣዩንም የምርጫ ዘመን ያለ ውክልና እንዲያሳልፍ የሚደረገው ሸፍጥ በፍፁም ተቀባይነት የለውም።
አዲስ ሪፖርተር – በወልቃይት-ጠገዴ-ሰቲት ሁመራ፣ በጠለምት፣ በራያ አለማጣና ኮረም-ኦፍላ አካባቢዎች እየተፈፀመ ያለውን የምርጫ መስተጓጎል እና መዋቅራዊ በደል አስመልክቶ ከአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ:-
የወልቃይት፣ የጠለምት እና የራያ አማራ ሕዝብ ለሩብ ክፍለ ዘመን የዘለቀ የህወሐት የአፓርታይድ አገዛዝ እና የዘር ማጥፋት ዘመቻን በጽናት ተቋቁሞ ከጥፋት ቢተርፍም፤ ዛሬም በፌዴራል መንግስቱ በተያዘው “ህወሐትን የማባበል ፖለቲካ” ሳቢያ ለከፋ ጥቃትና ስጋት ተጋልጦ ይገኛል።
ማንኛውም ማህበረሰብ ራሱን በራሱ የማስተዳደር፣ የመምረጥና የመመረጥ፣ እንዲሁም ፍትሃዊ የበጀት ክፍፍል የማግኘት መብቱ በዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችና በኢትዮጵያ ሕገ-መንግስት የተረጋገጠ ቢሆንም፤ በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖረው ሕዝባችን ግን በመንግስት እየተንጸባረቀ ከሚገኘው ለስላሳ ፖለቲካዊ ሴራ እና የአተርፍ ባይ ስሌት ህዝባችን መሰረታዊ መብቶቹን ተነፍጎ ይገኛል።
በተለይም ባለፉት ስድስት ዓመታት የማዕከላዊ መንግስቱ በጀትና የፖለቲካ ውክልና በመከልከል የተፈፀመው በደል ሕዝቡን ለከፋ ማህበራዊ ቀውስ ዳርጎታል። ይህ ሆን ተብሎ ሕዝብን ያለ በጀትና ውክልና የማስቀጠል አካሄድ፣ በሂደት ሕዝቡ ስለነጻነቱ ተስፋ እንዲቆርጥ የማድረጊያ ስትራቴጂ እንዳይሆን ንቅናቄያችን (አብን) ብርቱ ስጋት አለው።
በመሆኑም አብን በሚከተሉት አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም ማሳወቅ ይወዳል።
1) የምርጫ፣ የውክልና እና የበጀት እጦትን በተመለከተ
የወልቃይት-ጠገዴ-ሰቲት ሁመራ፣ እና የጠለምት ሕዝብ በህዝብና በሀገር መስዋዕትነት የተገኘውን ድል ለማጽናት በራሱ አቅም ሰላምና ጸጥታውን አስፍኖ የሚገኝ አካባቢ በመሆኑ፣ ምርጫ ላለማካሄድ ምንም አይነት ተጨባጭ ምክንያት ሳይኖር አንድ ሙሉ የምርጫ ዘመን ያለ በጀትና የፖለቲካ ውክልና እንዲያሳልፍ መደረጉ ታሪካዊ በደል መሆኑ እየታወቀ አሁንም በድጋሚ በተለያዩ ሰበቦች ሕዝቡን ከምርጫ በማግለል ቀጣዩንም የምርጫ ዘመን ያለ ውክልና እንዲያሳልፍ የሚደረገው ሸፍጥ በፍፁም ተቀባይነት የለውም።
2) የራያ አካባቢወችን በተመለከተም ህዝባችን ከመንግስት ጎን ቆሞ ባደረገው እልህ አስጨራሽ ትግል አካባቢወቹን ነጻ ቢያወጣም ቅሉ፤ መንግስት ለተደጋጋሚ ግዜ የራያ አለማጣና የኮረም-ኦፍላ አካባቢወችን ጥሎ በመውጣቱ ህዝቡን ለወያኔ የበቀል ዱላ አሳልፎ ሲሰጠው የቆየ ሲሆን፤ ዘንድሮም ይሄው “ህዝብን የማጋለጥና አሳልፎ የመስጠቱ ታሪክ” ለሶስተኛ ጊዜ በመቀጠሉና አካባቢወቹ ያለምንም መከላከል ለህወሐት ተላልፎ በመሰጠታቸው ከ60 ሽህ የሚበልጥ ህዝባችን ወደ ራያ ቆቦ፣ ወልድያና ሰቆጣ ከተሞች ተፈናቅሎ ምስቅስቅል ህይወት እየገፋ ይገኛል።
በመሆኑም መንግስት የአካባቢውን ጸጥታ የማስከበር ኃላፊነቱን በመወጣት ተፈናቃዮችን ወደ ቀያቸው ሊመልስና የፌዴሬሽን ምክር ቤት ያሳለፈው የበጀትና የውክልና ውሳኔ ተግባራዊ እንዲሆኑ ጥሪአችንን እያስተላለፍን የሚከተሉት የፍትህና የዴሞክራሲያዊ መብት ጥሰቶች በአፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኙ እንጠይቃለን:-
ሀ. የሕዝብ ሉዓላዊነት መሸርሸር (አንቀፅ 8)፦ ሕዝብን “አትወከልም” ማለት ሉዓላዊ ስልጣኑን በጉልበት መንጠቅ ነው።
ለ. የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት (አንቀፅ 39)፦
ያለ ተወካይ በምክር ቤቶች ድምፅ የሌለው ሕዝብ ራሱን የማስተዳደር መብቱ ተጥሷል።
ሐ. ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል መዛባት፦ ለሀገር ኢኮኖሚ ከፍተኛ አበርክቶ ያለውን ሕዝብ ከበጀት ድልድል ውጭ ማድረግ ፍፁም ኢ-ፍትሃዊነት ነው።
መ. የመንግስት ግዴታን አለመወጣት፦ የጸጥታ ችግርን እንደ ሰበብ በመጠቀም ሕዝብን ለሁለት የምርጫ ዘመናት (10 ዓመታት) ያለውክልና ማቆየት የመንግስትን ዘላቂ መፍትሄን ያለመሻት እና ከውጥረት አተርፋለሁ ባይነትን በጉልህ ያሳበቀ ሆኖ ይታያል።
ይህ በደል ካልታረመ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መፍረስን፣ መዋቅራዊ መድልዎና ጥቃትን፣ እንዲሁም ሕዝቡ በመንግስት ላይ ያዋለውን አመኔታ ጨርሶ እንዲያጣ በማድረግ ለማህበራዊ አለመረጋጋት ቀጥተኛ ምክንያት ይሆናል። ሕዝባችን በገዛ ሀገሩ እንደ “ሁለተኛ ዜጋ” ሆኖ ያለውክልና እንዲዘልቅ መደረጉ በሀገራዊ ምክክር ሂደቱ ላይም ጥቁር ጠበሳ የሚጥል ይሆናል።
ስለሆነም የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) የሚከተሉት ጥያቄዎች በአስቸኳይ ምላሽ እንዲያገኙ ይጠይቃል፦
1) የሕዝቡ ዴሞክራሲያዊ የምርጫ መብት የፌዴሬሽን ምክር ቤት በወሰነው መሠረት በአስቸኳይ እንዲከበር።
2) የተነፈገው መንግስታዊ የበጀት ድልድል ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲለቀቅ።
3) የራያ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው ተመልሰው ራሳቸውን የሚያስተዳድሩበት ሁኔታ እንዲመቻች እያሳሰብን፤
የፌዴራል መንግስቱ እና የኢትዮጵያ ብሄራዊ የምርጫ ቦርድ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔን ያለመሸራረፍ እንዲያስፈጽሙ እያሳሰብን፤ ይህ የማይሆን ከሆነ ጉዳዩን ወደ ሕግ ፊት በመውሰድ ሕዝባዊና ሕጋዊ ትግላችንን አጠናክረን የምንቀጥል መሆኑን ለሁሉም ወገን እናሳውቃለን።
የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን)
ሚያዚያ 12/2018 ዓ.ም
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addm






