ዲስ ሪፖርተር – የአሜርካና የኢትዮጵያ አዲሱ ስምምነት “ቋሚ ማዕቀፍ” መባሉ ግንኙነቱ በየጊዜው በሚቀያየሩ ፖለቲከኞች ፍላጎት ላይ ብቻ ሳይመሰረት፣ በቋሚነት በየዓመቱ ወይም በየተወሰነ ጊዜ የሚካሄድ የከፍተኛ ባለሥልጣናት ስብሰባ እንዲኖር የሚያደርግ መሆኑን የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ።
ስምምነቱን የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌድዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) እና የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የፖለቲካ ጉዳዮች ኃላፊ አሊሰን ሁከር ፈርመዋል።
ስምምነቱ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድና በቀይ ባህር ፖለቲካ ውስጥ ያላትን የማይተካ ሚና አሜሪካ ዳግም እውቅና የሰጠችበትና፣ ግንኙነቱን በዘላቂ መዋቅር ለመምራት የወሰነችበት የታሪክ ምዕራፍ እንደሆነም ዜናውን የተከታተሉ አመልክተዋል።
ዜናውን ይፋ ያደረጉት የሁለቱ አገራት መንግስታዊ ተቋማት እንዳሉት ኢትዮጵያና አሜሪካ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ቋሚ የሁለትዮሽ የምክክር ማዕቀፍ ስምምነት የተፈራመረሙት በዋሽንግተን ዲሲ ነው።
ይህ “ቋሚ ማዕቀድ” የተባለ ስምምነትና የሁለትዮሽ ምክክሩ ማዕቀፍ የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ዘላቂ በሆነ መንገድ የሚያስቀጥልና የሚያጠናክር መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
በዚህ ስምምነት ኢትዮጵያና አሜሪካ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ይበልጥ የሚያጠናክሩ የጋራ ትግበራ የሚሹ የትብብር አድማሶችን በማስፋት በሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና ዓለምአቀፋዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት ተስማምተዋል።
የተፈረመው የሁለትዮሽ መዋቅራዊ ምክክር በየዓመቱ አንዴ አዲስ አበባ ሌላ ጊዜ ዋሽንግተን ዲሲ የሚካሄድ ሲሆን የሁለቱ ሀገራት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ስብሰባውን በጋራ የሚመሩት ይሆናል። ኢትዮጵያ እና አሜሪካ የሁለትዮሹ መዋቅራዊ ምክክር ሦስት ምሰሶዎችን ያካተተ እንዲሆን ተስማምተዋል።
የመጀመሪያው የኢኮኖሚ ብልጽግናን፣ ንግድ እና ኢንቨስትመንት የሚዳስስ ሲሆን በዚህ ክፍል የሁለትዮሹን ኢኮኖሚያዊ እና የንግድ ትስስር የበለጠ ማጠናከርና ኢንቨስትመንት እና ንግድን ለማስፋት እንደሚሰራ ተገልጿል።
ሌላው የመከላከያ እና ጸጥታ ትብብርን የሚመለከት እንደሆነና የጸጥታ ጉዳይ ትብብርን ማጠናከርና በጋራ የደኀንነት ጉዳዮች ዙሪያ ተሳትፎን ማጠናከርን ያካትታል።
የመጨረሻው እና ሦስተኛው ምሰሶ ቀጣናዊ ሰላምና መረጋጋትን የተመለከተ ሲሆን በዚህ ክፍል የጋራ ጥቅምን እንዲሁም ቀጣናዊ ሰላምንና ደኀንነትን የሚያስጠብቁ አካሄዶችን በመፈተሽና በትብብር መሥራትን ያረጋግጣል።
ኢትዮጵያ እና አሜሪካ በዋሽንግተን ዲሲ የተፈራረሙት የሁለትዮሽ የምክክር ማዕቀፍ (Bilateral Ministerial Dialogue) በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ከመደበኛ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ባለፈ ተቋማዊ እና ቀጣይነት ያለው ለማድረግ ያለመ እንደሆነ ያመለከቱ፣ በዚህ ስምምነት በተለይ ከአሜሪካ አዲሱ የቀይ ባህር ስትራቴጂ አንጻር ኢትዮጵያ ቁልፍ ሚና እንዳላት ማረጋገጫ እንደሆነ ገለጸዋል።
ዌብሳይት፡ https://addisreporter.com/
ኢሜል፡ info@addisreporter.com
ቴሌግራም፡ https://t.me/addisreporter2
X፡ https://x.com/amejuju?s=21
https://web.facebook.com/addm






